የኢትዮ-ኤርትራ ግንኙነትን ለማጠናከር ታሪካዊ ሥራ እየተሠራ ነው- ፕሬዚደንት ኢሳያስ

የኤርትራ  ፕሬዚደንት ኢሳያስ አፈወርቂ  በኢትዮ-ኤርትራ  ግንኙነት ለማጠናከር  ታሪካዊ ሥራ  እየተሠራ  መሆኑን  ተናገሩ ።

ፕሬዚደንቱ ኢሳያስ በእሳቸው ለተመራው ከፍተኛ የልዑካን ቡድን በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት ዶክተር አብይ አህመድ ወደ ሥልጣን  ከመጡ በኋላ  የኢትዮጵያና ኤርትራ ሕዝቦች  ፍቅራቸውን  መግለጽ ችለዋል ብለዋል ።

ይህን የሁለቱን ሕዝቦች ፍቅር ሳያዩ በህይወት  ያለፉ ሰዎች እንዳሉ የጠቆሙት ፕሬዚደንት ኢሳያስ እኛ ይህን የሁለቱን ህዝቦች  ፍቅር በህይወት ዘመናችን ማየታችን እድለኛ ያደርገናል ብለዋል ።

የሁለቱ  አገራት  ሕዝቦች ታላቅ የሰላምና ወዳጅነት የተቀመጠለትን ግብ እንዲመታ  በጋራ መሥራት እንደሚገባ የገለጹት ፕሬዚደንት ኢሳያስ ከዚህ  በኋላ  የኢትዮጵያና ኤርትራ ህዝቦች ሁለት ህዝቦች ናቸው የሚል ሃቁን የማያውቅ ብቻ ነው ብለዋል ፕሬዚዳንቱ ።

ፕሬዚደንት ኢሳያስ አፈወርቂ በተጨማሪም የአዲስ  አበባ ከተማና አካባቢው ነዋሪ  በእሳቸው ለሚመራው የልዑካን ቡድን  ባደረገላቸው  ደማቅ የህዝብ አቀባበል እጅግ  ደስተኛ ከመሆናቸው  የተነሳ   ስሜታቸውን  መግለጽ  እንደተሳናቸው  ተናግረዋል  ።

በአጠቃላይ  ከልብ  የመነጨ  ፍቅራቸውን እየተገለጹ ላሉት  የኢትዮጵያ ኤርትራ ሕዝብም  ታላቅ  ምስጋና ከማቅረባቸውም  በተጨማሪ  ለሁለቱም አገር ህዝቦች የእንኳን ደስ አላቸሁ የሚል መልዕክት  አስተላልፈዋል   ።

ጠቅላይ  ሚንስትር  ዶክተር  አብይ አህመድ  በበኩላቸው  የአዲስ አበባና በአጠቃላይ  የኢትዮጵያ ህዝብ   ለኤርትራ  ልዑካን ቡድን  ላሳያው  ታላቅ ፍቅር  ምስጋና አቅርበዋል  ።