በአዲስ አበባ የሚገኘው የኤርትራ ኢምባሲ የኢትዮጵያና የኤርትራ መሪዎች በተገኙበት በዛሬው ዕለት በተካሄደ ደማቅ ሥነ ሥርዓት በይፋ ተከፍቶ ሥራ ጀምሯል ።
የኤርትራ ኢምባሲ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ላይ ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድና የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በተገኙበት የኤርትራ ብሔራዊ መዝሙር ተዘምሮ የኤርትራ ሰንደቅ ዓላማ በኢምባሲው እንዲውለበለብ ተድርጓል ።
ሁለቱ አገራት ወደ ግጭት ከገቡ በኋላ ለ20 ዓመት ያህል ዝግ የነበረው በአዲስ አበባ የኤርትራ ኢምባሲ በዛሬው ዕለት እድሳቱ ተጠናቆ እንዲከፈት ተደርጓል ።
ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ ከሳምንት በፊት በአሥመራ ባደረጉት ጉብኝት ከኤርትራው ፕሬዚዳንት ጋር ሁለቱ አገራት ኢምባሲዎቻቸውን እንዲከፍቱ ያደረጉትን ስምምነት ተከትሎ ነው የኤርትራ ኢምባሲ እንዲከፈት የተደረገው ።
ኢትዮጵያም በስምምነቱ መሠረት በቅርቡ በአሥመራ ኢምባሲዋን እንደምትከፍትም ተገልጿል ።