ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ከአሜሪካ ኮንግረስ አባል ክሪስ ስሚዝ የልዑካን ቡድን ጋር ተወያዩ

የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የአሜሪካ ኮንግረስ አባል በሆኑት ክሪስ ስሚዝ ከተመራው የልዑካን ቡድን ጋር ተወያዩ ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በክሪስ ስሚዝ የተመራ የልዑካን ቡድንን በፅህፈት ቤታቸው ተቀብለው ማነጋገራቸውን ስብሰባውን የተከታተሉት የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ልዩ ሀላፊ አቶ ፍፁም አረጋ በትዊተር ገፃቸው አስታውቀዋል።

በውይይታቸውም በኢትዮጵያና አሜሪካ መካከል ስላለው የሁለትዮሽ እና በቀጠናዊ ጉዳዮች ዙሪያ መወያየታቸውንም ገልፀዋል።

በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ በአሜሪካ ኮንግረስ አባል ክሪስ ስሚዝ ለተመራ ልዑካን ቡድን በኢትዮጵያ እየተካሄደ ስላለው የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ዙሪያ ገለጻ አድርገውላቸዋል።

በአሜሪካ ኮንግረስ የውጭ ጉዳይ ኮሚቴ የአፍሪካ ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ የኮንግረስ አባሉ ክሪስ ስሚዝ የተመራ የልዑካን ቡድን በኢትዮጵያ የስራ ጉብኝት ለማድረግ ዛሬ ነበር አዲስ አበባ የገባው።

ልዑኩ ከኢፌዲሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁ ጋርም ተገናኝቶ ተወያይቷል።

በቆይታቸውም በኢትዮጵያ እየተካሄደ ስላለው ለውጥ አድናቆት ያላቸው መሆኑን የአሜሪካ ኮንግረስ አባል ክሪስ ስሚዝ ተናገረዋል። (ኤፍ.ቢ.ሲ)