የታላቁ ህዳሴ ግድብ ሠራተኞች ከደሞዝ ጭማሪ ጥያቄ ጋር በተያያዘ የሥራ ማቆም አድማ አደረጉ

የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድብ ግንባታ ሰራተኞች በደመወዝ ጭማሪ ጥያቄና በአገልግሎት አሰጣጥ ችግር ምክንያት ላለፉት ሶስት ቀናት የስራ ማቆም አድማ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል፡፡

ሰራተኞቹ በግድቡ ግንባታ ላይ አሻራቸውን እያሳረፉ ቢሆንም የሚከፈላቸው ክፍያ አናሳ መሆኑ ኑሯቸውን ከባድ እንዳደረገባቸው ተናግረዋል፡፡

በግንባታው ተቋራጭ በኩል ከደመወዝ ክፍያ ማነስ በተጨማሪ የሠራተኛ አያያዝ፣ የምግብ ቤት የጥራት ችግርና የዋጋ መናር የስራ ማቆም አድማ እንዲያደርጉ እንዳስገደዳቸው ተናግረዋል፡፡

የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ኤፍሬም ወልደ ኪዳን ሠራተኞቹ ላለፉት ሶስት ቀናት የስራ ማቆም አድማ ላይ መሆናቸውን አረጋግጠዋል፡፡

ሰራተኞቹ ያቀረቡትን ችግር ለመፍታት በማወያየት ላይ መሆናቸውንም ገልፀዋል፡፡

ከሰዓት በኃላ የግንባታ ተቋራጩን ጨምሮ በሚደረግ የጋራ ውይይት ችግሩ ይፈታል ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል ማለታቸውን ዘግቧል፡፡(ምንጭ:ኢቢሲ)