በአማራ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ የሚመራ ልዑክ ነገ ወደ ኤርትራ ያቀናል

በአማራ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባዔ የሚመራ ልዑክ ነገ መስከረም 03/2011 ወደ ኤርትራ እንደሚያቀና የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ አስታወቀ፡፡

የቢሮው ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሱ ጥላሁን እንደገለጹት በምክር ቤት አፈ ጉባዔ የሚመራ የሃይማኖት አባቶችን ያካተተ ልዑክ ወደ ኤርትራ የሚያቀናው የሁለቱን አገራት የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትና ትስስርን ለማጠናከር ነው፡፡

ሁለቱ ሃገራት የፈጠሩትን ሰላም ተከትሎ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን ለማጠናከር ስምምነት ላይ መደረሱን ተናግረዋል፡፡

የኤርትራ ባለስልጣናት የሁለቱ አገሮች የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ይበልጥ እንዲጠናከር ወደ አማራ ክልል ለመምጣት ፍላጎቱ እንዳላቸው አቶ ንጉሱ ገልጸዋል፡፡

የአማራ ክልልም ተመሳሳይ ፍላጎት በማሳደሩ የኤርትራን ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂን ጨምሮ የኤርትራ ልዑካን ወደ ክልሉ እንዲመጡ መጋበዛቸውን ነው ዳይሬክተሩ የተናገሩት፡፡ /የኢትዮጵያ ፕሬስ ኤጄንሲ/