ፍርድ ቤቱ በኢትዮጵያ ሲቪል አቬይሽን ዘጠኝ ተጠርጣሪዎች ላይ የሰባት ቀን ጊዜ ፈቀደ

መርማሪ ፖሊስ በኢትዮጵያ ሲቪል አቬይሽን ዘጠኝ ተጠርጣሪዎች ላይ ከጠየቀው የ14 ቀን ጊዜ ውስጥ ፍርድ ቤቱ የሰባት ቀን ጊዜ ፈቀደ፡፡

የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ አራዳ ምድብ ተረኛ ወንጀል ችሎት የዘጠኙ ተጠርጣሪዎች ጉዳይ ዛሬ ተመልክቷል፡፡

መርማሪ ፖሊስ እስከአሁን በተሰጠው ጊዜ ውስጥ የተጠርጣሪዎቹን ቃል መቀበል፣ አሻራ እና ፎቶ ማንሳት እንዲሁም የሦስት ምስክሮችን ቃል የመቀበል ስራን መስራቱን ገልጿል፡፡

በቀጣይም ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ቢሮ የተጠርጣሪዎቹን የስልክ ልውውጥ ማስረጃ ለመሰብበሰብ በአየር መንገዱ ላይ በተጠርጣሪዎቹ ምክንያት የደረሰው ኪሳራ ማስረጃ ለመሰብሰብ ያልተያዙ ተጠርጣሪዎች ለመያዝ በጥቅሉ ከወንጀሉ ጋር ግንኙነት ያላቸውን ማስረጃዎች ለማምጣት እና ተጨማሪ የምስክር ቃል ለመቀበል የ14 ቀን ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ይሰጠኝ ሲል ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ በበኩላቸው በጠበቃቸው አማካኝነት የጠየቅነው የመብት ጥያቄ የሥራ ማቆም አድማ ህገመንግስታዊ መብታችን ነው በማለት ፖሊስ ላቀረባቸው ምክንያቶች ተገቢነት የሌለው መሆኑንም በጠበቃቸው አማካኝነት ገልጸዋል፡፡

እንዲሁም በራሳቸው ከክልል ሰራተኞች ጋር የሚያገናኛቸው ነገር ያለመኖሩና በነሐሴ 18 2010 ስራ እንደሚያቆሙ በደብዳቤ ማሳወቃቸውን የአቬሽኑ ሰራተኞች እንደመሆናችን የአየር መንገዱ ኪሳራ አይመለከተንም ስለዚህም በዋስ ወጥተን ለስራው አስፈላጊ በመሆናችን ስራ ላይ ሆነን ፖሊስ ምርምመራውን መቀጠል ይችላል በማለት ዋስት ና እንዲፈቀድላቸው ጠይቀዋል፡፡

ፖሊስ በበኩሉ ተጠርጣሪዎች በውስጣቸው መልዕክት ያዘሉና ከሌሎች አካላት ጋር በመሆን ሴራ የታከለበት እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ነበር እንዲሁም ዲያስፖራው መግቢያ ሰዓት ላይ ዲያስፖራውን በማወክ የአየር መንገድ በማስተጓጎል ሆነ ብለው ሌሎችንም ሲያነሳሱ ሰራተኞችን ገብተው ስራቸውን እንዳይሰሩ ሲከለክሉ እንዲሁም ገቢና ወጪ አውሮፕላኖች እንዳያርፉ እንዳይወጡ ቆዩ፤ ዘግየት በሉ በማለት አየርመንገዱ ከፍተኛ ኪሳራ እንዲደርስበት ስለማድረጋቸው የምስክር ቃል ተቀብያለው ሲል ጥያቄያቸውን ተቋውሟል፡፡

የግራ ቀኙን ያደመጠው ፍርድ ቤቱ የዋስትና ጥያቄያቸውን በማለፍ ፖሊስ ከጠየቀው ከ14 ቀን ጊዜ ውስጥ የሰባት ቀን ጊዜ በመፍቀድ ለመስከረም ስምንት ቀን ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ (ኤፍ.ቢ.ሲ)