አቃቢ ህግ በሰኔ 16ቱ የቦምብ ፍንዳታ ላይ ቦምብ በማፈንዳት ወንጀል አምስት ግለሰቦች ላይ ክስ መሰረተ

ጠቅላይ አቃቢ ህግ በሰኔ 16ቱ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በተደረገው የድጋፍ ሰልፍ ላይ ቦምብ አፈንድተዋል ያላቸው አምስት ግለሰቦች ላይ ክስ መሰረተ፡፡

አምስቱ ግለሰቦች ጌቱ ግርማ፣ ብርሃኑ ጃፈር፣ ጥላሁን ጌታቸው፣ ባህሩ ቶላ እና ደሳለኝ ተስፋዬ ናቸው አቃቢ ህግ ቦምብ በማፈንዳት ወንጀል ክስ የመሰረተባቸው፡፡

ክሱ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተረኛ ወንጀል ችሎት የተከፈተ ሲሆን ክሱን ለእያንዳንዳቸው በችሎት እንዲደርስ ይደረጋል ተብሏል፡፡

የጠቅላይ አቃቢ ህግ እንደሚያመላክተው አንደኛ ተከሳሽ ጌቱ ግርማ ከሁለተኛ ተከሳሽ ጋር ሱሉልታ ላይ በመገናኘት ሰልፉን የጠራው ገለልተኛ ወገን ሳይሆን ኢህአዴግ ነው ኤችአር 128 የተባለውን በአሜሪካ ኮንግረስ የተላለፈውን ውሳኔ ተግባራዊ እንዳይሆን ያደርጋል የሚል ምክንያቶችን በመግለጽ ቦምቡን በመወርወር እንዲበተን እናድርግ በማለት እንዲዘጋጅ መግለጹን በክሱ ተመላክቷል፡፡

ለሦስተኛ ተከሳሽ ደውሎም ቦምብ የሚወረውር ሰው አንዲፈልግ ተልዕኮ መስጠቱ በክሱ ተጠቅሷል፡፡

ሁለተኛ ተከሳሽ ብርሃኑ ጃፈር ደግሞ በሚያዝያ ወር 2010 ዓመተምህርት ሁለት ኤፍ 1 እና አንድ የጭስ ቦምብ ያለው መሆኑን ለአንደኛ ተከሳሽ መግለጹን የጠቀሰው አቃቤ ህግ ሱሉልታ ከተማ ተገናኝተው ቦምቡን የድጋፍ ሰልፉ ላይ በመወርወር ጥቃት ለማድረስ በመነጋገር ቦምቡን መወርወር የሚችሉ ልጆች እንዲዘጋጁ ከአንደኛ ተከሳሽ ጋር ተነጋግረዋል ሲል አቃቤ ህግ በክሱ ጠቅሷል፡፡

ሦስተኛ ተከሳሽ ጥላሁን ጌታቸው በድጋፍ ሰልፉ ላይ ቦምብ እንዲያፈነዳ በአንደኛ ተከሳሽ ተገልጾለት ለአራተኛ ተከሳሻ በመደወል ቦምብ ለመወርወር ማቀዱን በመግለጽ በጉዳዩ ላይ ለመወያየት እንዲገናኙ ማድረጉ ተገልጿል፡፡

አራተኛ ተከሳሽ ባህሩ ቶላ በአንደኛ ተከሳሽ አማካኝነት መስቀል አደባባይ ቦምቡን ለመወርወር ማቀዱን በመጥቀስ በሁኔታው ለመወያየት አስኮ የተቀጣጠሩ ሲሆን ከዚያም ቡራዩ ላይ በአምስተኛ ተከሳሽ ቤት ተገናኝተዋል፡፡

ከተገናኙ በኋላም በአምስተኛ ተከሳሽ ቤት ያደሩ ሲሆን አንደኛ እና ሁለተኛ ተከሳሾች በሰኔ 16 2010 ዓመተምህረት ከንጋቱ 11፡00 ሰዓት ላይ ሁለተኛ ተከሳሽ በሚያሽከረክረው የሰሌዳ ቁጥር ኮድ2 262335 አዲስ አበባ በሆነ መኪና ውስጥ ሁለት ኤፍ 1 ቦምብ እና አንድ የጭስ ቦምብ በመያዝ አንደኛ ተከሳሽ ቤት ማስቀመጣቸውን በክሱ ተጠቅሷል፡፡

ያስቀመጡትን ቦምብም በዚሁ ተሸከርካሪ ጭነው አዲስ አበባ ውንጌት አካባቢ ከሦስተኛ፣ ከአራተኛ እና ከአምስተኛ ተከሳሽ ጋር በመገናኘት ፒያሳ አካባቢ የገቡ ሲሆን በምን መልኩ ጥቃቱን ማድረስ እንዳለባቸው መወያየታቸውም ተገልጿል፡፡

እንዲሁም በዕለቱ የዶክተር አብይ አህመድ ምስል ያለበትን ቲሸርት ገዝተው እንዲለብ ሱ በማድረግ በተጠቀሰው መኪና ቴዎድሮስ አደባባይ ድረስ በመሸኘት ቦምቡ እንዲፈነ ዳ ተልዕኮ በመስጠት የተመለሱ ሲሆን ሦስተኛ፣ አራተኛ እና አምስተኛ ተከሳሾች በተሰጣቸው ተልዕኮ መሰረት ከሰልፈኞች ጋር በመቀላቀል ሦስተኛ ተከሳሽ በሐራምቤ አቅጣጫ በማድረግ ወደ መስቀል አደባባይ መግባቱ የተጠቀሰ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር አድርገው ሲጨርሱ ከመድረኩ በቅርብ ርቀት ላይ በመገኘት ቦምቡን ወርውሮ ማፈንዳቱን አቃቢ ህግ ጠቅሷል፡፡

በዚህም ሙሳ ጋዲሳና ዮሴፍ አያሌው የተባሉ ግለሰቦች በፍንዳታው ህይወታቸው ማለፉን በክሱ ተጠቅሷል፡፡

በፍንዳታው ከ163 በላይ በሆኑ ንጹሃን ግለሰቦች ላይ ከባድና ቀላል ጉዳት አድርሰውባቸዋል ተብሏል፡፡

አራተኛ ተከሳሽ ደግሞ ይዞት የነበረውን ኤፍ 1 ቦምብ ናኒ ህንጻ ፊትለፊት ትንሹ ሜዳ ላይ የወረወረ ሲሆን ነገርግን የተወረወረው ቦምብ ሳይፈነዳ መቅረቱ ተገልጿል፡፡

ቦምቡ ስለመክሸፉም ለአንደኛ ተከሳሽ በስልክ ሪፖርት በማድረግ ከአካባቢው እንዲሰወር በተሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ከአካባቢው ተሰውሯል፡፡

በጥቅሉ ተከሳሾቹ በቡድን በመደራጀት ለጊዜው በቁጥጥር ስር ባልዋሉ ግብረ አበሮቻቸው መሰረት በተሰጣቸው ተልዕኮ በድጋፍ ሰልፉ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ ጥቃት ለመሰንዘር ባደረጉት የመግደል ሙከራ በሰው ህይወትና በአካል ላይ ጉዳት ያደረሱ በመሆኑ ባደረሱት የሽብርተኝነት ድርጊት መፈጸም ወንጀል አቃቢ ህግ ክስ መስርቶባቸዋል፡፡ (ኤፍ.ቢ.ሲ)