የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦብነግ) በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ስምምነት ላይ ደረሰ

የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦብነግ) በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ስምምነት ላይ መድረሱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁ አስታወቁ።

የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃ አውጪ ግንባርና የኢትዮጵያ መንግስት በዛሬው ዕለት በአስመራ ባደረጉት ድርድር ስምምነት ላይ መድረሳቸው ተነግሯል።

በዚህም ለረጅም አመታት የትጥቅ ትግልን አማራጭ አድርጎ ሲንቀሳቀስ የቆየው የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻ አውጪ ግንባር ወደ ሀገር ቤት ተመልሶ በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ስምምነት ላይ መድረሱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ገልፀዋል።

የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦብነግ) በቅርቡ ልዑኩን ወደ ሀገር መላኩ የሚታወስ ነው።

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ያቀረቡትን የሰላም ጥሪ ተከትሎ ኦነግ፣ አርበኞች ግንቦት 7 እንዲሁም የትግራይ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደምህት) የትጥቅ ትግል በማቆም ወደ ሀገር ቤት መግባታቸው ይታወቃል።(ኤፍ.ቢ.ሲ)