የኢፌዴሪ ፕሬዚደንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ ከኃላፊነት የመልቀቅ ጥያቄ ተቀባይነት አገኘ

የህዝብ ተወካዮችና የፌደሬሽን ምክር ቤቶች  በዛሬው ዕለት  ባደረጉት  2ኛ ልዩ  የጋራ ስብሰባ   የኢፌዴሪ ፕሬዚደንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ  ለርዕሰ  ብሔርነት ኃላፊነት   ለመልቀቅ  ያቀረቡት ጥያቄን  ተቀብለዋል ።

ፕሬዚዳንት ዶክተር  ሙላቱ  በዛሬው ዕለት  በጋራ ምክር ቤቶቹ ላይ በመገኘት የሥራ  ስንብት ወይም  ከሃላፊነት የመልቀቅ ጥያቄያቸውን አቅርበዋል ።

ፕሬዚዳንቱ ለምክር ቤቶቹ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት አምስት ዓመት በፊት  ሁለቱም  ምክር ቤቶች ባደረጉት ስብሰባ  በሙሉ ድምጽ በፕሬዚደንትነት እንድመረጥና  በሥራ  ዘመኔ  ሙሉ ትብብር  ላደረጉላቸው  የኢትዮጵያ መንግሥትና ህዝብ የታላቅ  ምስጋና አቅርበዋል ።

በአምስት ዓመት ውስጥ አቅሜና በፈቀደ ሁሉ  የተጣለብኝን ኃላፊነት  በታማኝነት እንደፈጸምኩ  ይሰማኛል ብለዋል  ፕሬዚደንቱ ።

ከስድስት ወራት  በፊት  አገሪቷ  በመስቀለኛ  መንገድ ነበረች ያሉት  ፕሬዚደንት አሁን  ግን በአገሪቱና በህዝቦቿ ዘንድ  የተስፋ  ጎህ  ቀዶ ቀዷል  በማለት ገልጸዋል ።

ፕሬዚዳንቱ በንግግራቸው ከሰባት ወራት  በፊት  በአገሪቱ  እንደዚህ ዓለምን ያስደመመ ለውጥ ይመጣል ብሎ ያመነም  ያሰበም እንደሌለ   ጠቅሰዋል ።

በአገሪቱ  የፖለቲካ  ምህዳሩን  ለማስፋት   እስረኞች እንዲፈቱ  በውጭ  በትጥቅ ትግል የሚገኙ  ኃይሎች  በሰላም  ወደ አገራቸው  ገብተው በሰላም  የሓሳብ  ትግል መፈቀዱ ሌላው  የኢትዮጵያውያንን ብቻ ሳይሆን የዓለም አቀፍ ማህበረሰብን ያሰደነቁ ተግባራት እንደነበሩ ጠቁመዋል ።

ኢትዮጵያና ኤርትራም  ከነበሩበት ወጥተው ሕዝቦቻቸው  በፍቅር፣ በአንድነትና በመከባበር ላይ የተመሠረተ ግንኙነት  መፍጠር መቻላቸው ሌላው  የለውጥ መገለጫ መሆኑን ፕሬዚደንቱ  በንግግራቸው አስረድተዋል ።

በአገራዊ ለውጡ ቀላል የሚመስሉ ቢሆንም  ለነገ አገራዊ  ለውጥ ትልቅ ስንቅ እንደሚሆንም   ፕሬዚደንቱ አስገንዝበዋል ።

በአገሪቱ  በረጅም ጊዜ  የታቀዱ  ረዕዮችን ለማሳካትና ዘለቂነት  ለማስጠበቅ  ህዝቡን  በማስተባበረ መሥራት  እንደሚያስፈልግም ፕሬዚደንቱ ጠቁመዋል  ።

በአገሪቱ  የሰፈነውን ድህነትን፣ ኃላቀርነትና መሃይምነትን በማስወገድም  የዜጎችን  ተጠቃሚነትን ማሳደግም ይገባል  ብለዋል ።

በአገሪቱ   አሁን የተጀመረውን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታን  በዘላቂነት  ለማጠናከርን   ጠንካራና ተጠያቂ ተቋማትን  መፍጠር እንደሚያስፈልግም  ፕሬዚዳንቱ አንስተዋል ።

ዜጎች  በጥርጣሬ  ላይ የተመሠረተ  የፖለቲካ  አውድ አገሪቱን  ወደ  ሌላ ሁኔታና አደጋ   የሚወስድ  በመሆኑም   ማንኛውንም የፖለቲካና  የኢኮኖሚ  ጥያቄ  በብሔር መነጽር   ብቻ  ማየት መቀጠል የለብንም ብለዋል ፕሬዚደንቱ  በንግግራቸው ።

  ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ  በርዕሰ ብሔርነታቸው  ወቅት ለውጡን ለማየትና አካል መሆን በመቻላቸው  ኩራት  እንደሚሰማቸውም ገልጸዋል ።

በመጨረሻም  ፕሬዚዳንቱ ይዤ  የቆየሁትን  አገራዊ ኃላፊነት  ለቀጣዩ ትውልድ  ለማስተላለፍ  ውሳኔ ላይ   የደረስኩ በመሆኔ የተከበሩት  ምክር ቤቶች  ኢፌዴሪ ፕሬዚደንትነት ኃላፊነቴ  እንዲያሰናብተኝ  እጠይቃለሁ ብለዋል ።