ጀግኒት ሀገር አቀፍ የሴቶች የሰላም ኮንፈረንስና ንቅናቄ ፕሮግራም ሊጀመር ነው

 “ጅግኒት አለመች፣አቀደች አሳካች” በሚል መሪ ቃል የሚከናወነውን ሀገራዊ የህብረተሰብ ንቅናቄ ዝግጅትን አስመልክቶ ዘጠኙ ሴት ሚኒስትሮችና የሁለቱ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤና ምክትል አፈ ጉባኤ በተገኙበት ትናንት ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል።

ከሁሉም ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ሴቶች የሚሳተፉበት ሀገር አቀፍ የሴቶች የሰላም ኮንፈረንስ የፊታችን ጥቅምት 26 ቀን 2011 ዓም እንደሚካሄድም ተገልጿል።

በመግለጫው ላይ ንግግር ያደረጉት የሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስትር ወይዘሮ ያለም ፀጋይ ፥ ኮንፈረንሱ በሀገሪቱ ውስጥ ዘላቂ ሰላም በማረጋገጥ፤ የሴቶችና ህፃናትን የአደጋ ተጋላጭነት በመቀነስ መብትና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እና ሴቶች ሰላም መከበር ያላቸውን አበርክቶ ለማሳደግ ነው ብለዋል።

እንዲሁም የሴቶችና ህፃናትን ደህንነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ በየአከባቢው ሴቶች ለሰላማቸው ጠንክረው እንዲሰሩ ለማድረግም ነው ብለዋል።

ንቅናቄው በሀገሪቱ የሴቶችን ጥንካሬ ከተተኪነት በላይ ራሳቸው ለተሻለ ነገር የሚያበቁ እና ብቁ ትውልድ የሚያፈሩ መሆናቸውን ለማሳየት ያስችላል ተብሏል።

በአሁን ሰዓት ሴቶች በሀገሪቱ ልማትና እድገት ላይ በየደረጃው እየተወጡ ያለው ከፍተኛ አስተዋፅኦ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በማሳወቅና በማሳየት ክብርና እውቅና ማግኘት እንዲችሉ ያደርጋል ነው የተባለው።

ከንቅናቄው በኋላ የሴቶች የልማት ጥምረት ይመሰረታል የተባለ ሲሆን፥ ይህም በሴቶችና ህፃናት ዙሪያ የሚንቀሳቀሱ አካላት ለማጠናከር፣ በዘላቂ ሰላም ማረጋግጥና ሴቶች በልማቱ ያላቸው ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ዙሪያ የራሱ ድርሻ እንደሚኖረው ተጠቁሟል።

ሀገሪቱ ዴሞክራሲ እንዲሰፍንና በሀገሪቱ የተጀመረውን ለውጥ ለማፋጠንም ንቅናቄው አስተዋፅኦው የጎላ ይሆናል ተብሏል።

በኮንፈረንሱ ለሚኒስትሮቹ አሁን ያለውን የሚኒስትሮች ቁጥር ለማስቀጠል ምን ታስቧል ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የሰላም ሚኒስትሯ ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ ብዙ አቅም ያላቸው ሴቶች እንዳሉና ንቅናቄው እስከ ወረዳ ድረስ የ

ሚካሄድ በመሆኑ አቅም ያላቸውን ሴቶች ወደ ከፍተኛ የስልጣን እርከኖች ማምጣት ይቻላል ብለዋል።  (ኤፍ.ቢ.ሲ)