በኦሮሚያ ክልልና በአዲስ አበባ ከተማ መካከል ላለው የአስተዳደር ወሰን ውዝግብ መፍትሄ የሚያቀርብ ኮሚቴ ተዋቀረ

በኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት እና በአዲስ አበባ ከተማ መካከል ያለውን የአስተዳደር ወሰን ውዝግብ በተመለከተ ዘላቂ መፍትሄ የሚያስቀምጥ ኮሚቴ ተቋቋመ።

የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ባወጣው መግለጫ በኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት እና በአዲስ አበባ ከተማ መካከል ያለው የአስተዳደር ወሰን በአግባቡ አለመካለሉን አንስቷል።

ይህን ችግር በዘላቂነት በመፍታት የአስተዳደር ወሰን አካባቢዎች የግጭት እና የንትርክ አጀንዳ ከመሆን ይልቅ የልማት እና የፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚረጋገጥባቸው አካባቢዎች እንዲሆኑ በማሰብ ችግሩን በጥናት ላይ የተመስርቶ ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠት ከኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት እና ከአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር የተውጣጣ የጋራ ኮሚቴ ተዋቅሮ ጥናቶች ቢደረጉም የጥናቱ ውጤት ላይ ጉዳዩን መቋጨት አለመቻሉን ነው ፅህፈት ቤቱ ያመለከተው።

ይህም በመሆኑ የኦሮሚያ ክልል እና የአዲስ አበባ ከተማ ወሰን ጉዳይ አወዛጋቢ ሆኖ ቀጥሏል ብሏል።

በኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት እና በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር መካከል እልባት ያላገኘ የአስተዳደር ወሰን ይገባኛል ጥያቄ መፍትሄ ሳይሰጠው የጋራ መኖሪያ ቤቶች እጣ መውጣቱም ውዝግብ ማስነሳቱን ገልጿል።

በአዲስ አበባ ከተማ እና በኦሮሚያ ክልል መካከል ያለውን የአስተዳደር ወሰን ጥያቄን በዘላቂነት ለመፍታት ከዚህ በፊት የተጠኑ ጥናቶችን መሰረት በማድረግ እና ህዝቡን በማሳተፍ ዘላቂ መፍትሄ ማስቀመጥ ወሳኝ ሆኖ መገኘቱን የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት አስታውቋል።

በዚህም መሰረት ስምንት አባላት ያሉት ከፌደራል መንግስት፣ ከኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት እና ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳድር የተውጣጡ አባላትን የያዘ ኮሚቴ ተዋቅሮ ለጉዳዩ መፍትሄ የሚሆን ምክረ ሀሳብ እንዲያቀርቡ አቅጣጫ ተቀምጧል ነው ያለው።

የኮሚቴው አባላትም፦

1. ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል፦ የሰላም ሚኒስትር (የኮሚቴው ሰብሳቢ)

2. ወይዘሮ ጠይባ ሀሰን፦ የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ምክትል ርእሰ መስተዳድር (የኮሚቴው አባል)

3. አቶ አህመድ ቱሳ፦ በኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ምክትል ርእሰ መስተዳድር ማእረግ የከተማ ልማት ክላስተር አስተባባሪ (የኮሚቴው አባል)

4. ዶክተር ግርማ አመንቴ፦ በኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ምክትል ርእሰ መስተዳድር ማእረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪ (የኮሚቴው አባል)

5. ኢንጂነር ታከለ ኡማ፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ (የኮሚቴው አባል)

6. አቶ እንዳወቅ አብ፦ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማእረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ (የኮሚቴው አባል)

7. ዶክተር ሰለሞን ኪዳኔ፦ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማእረግ የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ (የኮሚቴው አባል)

8. አቶ ተስፋዬ በልጅጌ፦ የአዲስ አበባ ከተማ የከንቲባው የህዝብ አደረጃጀት አማካሪ (የኮሚቴው አባል)