በደረሰባቸው ጥቃት ከቡራዩ ለተፈናቀሉ 100 ዜጎች ድጋፍ እየተደረገ ነው

በኦሮሚያ ክልል ቡራዩ አካባቢ እየተንቀሳቀሱ ያሉ የሁከት ሃይሎች ባለፉት አራት ቀናት ማንነትን መሰረት ያደረገ ጥቃት አድርሰዋል።

እነዚህ ሃይሎች መኖሪያቸውን በስፍራው ባደረጉ ዜጎች ላይ ማንነትን መሰረት ያደረገ ጥቃት መፈጸማቸውን የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ዜጎች አስታውቀዋል።

ጥቃቱ እስከተፈጸመበት እስካለፈው ሰኞ ድረስ፥ የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ዜጎች በቡራዩ አካባቢ ከሶስት እስከ አስር አመት መኖራቸውን ይገልጻሉ።

ባለፉት አራት ቀናት ግን አመታትን ከኖሩበት አካባቢ የሚያፈናቅል ንብረታቸውን ትቶ የሚያሸሽ ጥቃት ደረሰብን ይላሉ፥ በቡራዩ አካባቢ ልዩ ስፍራው ቤሩ ተብሎ በሚጠራ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ዜጎች።

የጥቃቱ ሰለባዎች እንደሚሉት ድርጊቱ በጥቂት ሁከት እና ዘረፋን በሚሹ ሃይሎች ከመፈፀሙ በስተቀር፥ ከሌላው የቡራዩ ከተማ ነዋሪ የኦሮሞ ህዝብ የደረሰባቸው በደል እንደሌለም አስረድተዋል።

በጥቃቱ ምክንያት ይኖሩበት የነበረውን አካባቢ ለቀው ከተፈናቀሉ ዜጎች መካከል፥ 112 የሚሆኑት በአዲስ አበባ ጉለሌ ክፍለ ከተማ በአንድ የቀበሌ ወጣቶች መዝናኛ ውስጥ በጊዜያዊነት ተጠልለው ይገኛሉ።

ለእነዚህ ዜጎች በአሁኑ ወቅት ተጠልለው በሚገኙበት አካባቢ የምግብ እና አልባሳት ድጋፍ እየተደረገ ነው -(ኤፍ ቢ ሲ)