የወገኖቻችን ሞት ፣ መፈናቀልና ጉዳት በማስቆም ለአገራዊ አንድነት ሊተጋ እንደሚገባ የኃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች ገለጹ

የወገኖቻችን ሞት ፣ መፈናቀልና ጉዳት በአፋጣኝ  በማቆም ሁሉንም  ወገን ቅድሚያ ለአገራዊ አንድነት፣ ሰብዓዊ ክብርና ሰላም ሊተጋ እንደሚገባ የኢትዮጵያ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች  ገለጹ ።

የኢትዮጵያ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች በዛሬው ዕለት በሠጡት መግለጫ እንደገለጹት በአገሪቱ የሚታየውን አለመረጋጋትና ውጥረት በማርገብ ሰላምና አንድነትን  ለማጠናከር  በሚያስችለው “ ሰላም ለሁላችን ፣ በሁላችን!” በሚል መሪ ቃል የሚደረገው የሰላም ጉዞ  መጀመሩን ገልጸዋል ።

በተጀመረው የሰላም ጉዞና ምክክር መድረኩ በተለያዩ ክልሎች የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮችና የተለያዩ  የህብረተሰብ ክፍሎች  ጋር በመገናኘት  በወቅታዊ የአገሪቱ ሁኔታ ችግሮችና መፍትሔዎች ላይ  ምክክር ማድረግ ተችላል ብሏል መግለጫው ።

ለዘመናት በመከባባር የኖሩት ኢትዮጵያውያን ወገኖች በመካከላቸው አለመከባበርና አለመተማመን የሚፈጥሩ ተጨባጭ ችግሮችም እየታዩ    መሆናቸውን መገንዘባቸውን  ባወጡት መግለጫቸው አትተዋል ።

በአገሪቱ ሁሉም አካባቢዎች በሚፈጠረው  ግጭት በየዕለቱ የንጹሓን ዜጎች ደም  በከንቱ  እየፈሰሰ ፣ ወገኖችም እየተፈናቀሉና ለእንግልት እየተጋለጡም መሆኑን  መግለጫው አብራርቷል ።

መግለጫው በተጨማሪም እየተስተዋሉ ያሉት ግጭቶችና አለመረጋጋቶች መነሻቸው የትኛውም ይሁን ለአገር ሰላምና ወገን ደህንነት በማሰብ ችግሮችን በወይይት መፍታት እንደሚያስፈልግም ተጠቁሟል ።

በኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት  ጉባኤ  የበላይ አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች  በጋራ  በመሆን  ለመላው ሰላም ወዳድ ኢትዮጵያውያን ሁሉ የሰላም መልዕክትና ተማጽኖ የሚያስተላልፍ ባለ ስምንት ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት  ጥሪያቸውን አቅርበዋል ።