በሶማሌ ክልል የተጀመሩ የልማት ስራዎች በአዲሱ ዓመትም ለማጠናከር በትኩረት ይሰራል- አቶ ሙስጠፌ ሙሃመድ

በሶማሌ ክልል የተጀመሩ የህግ የበላይነት ማስከበርና የልማት ስራዎች በአዲሱ ዓመትም ተጠናክረው ህዝቡ ባገኘው ነፃነት እንዲጠቀም በትኩረት እንደሚሰራ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ሙስጠፌ ሙሁመድ አስታወቁ።

የዘመን መለወጫን በዓልን አስመልክተው ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ እንደገለጹት በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት በክልሉን ሆነ በሀገሪቱ የተለያዩ አከባቢዎች ግጭትና የዜጎች አለመረጋጋት የተከሰተበት ጊዜ ነበር።

ችግሩን በመንግስትና ህዝቡ ጥረት በፍጥነት ማስተካክል መቻሉን ተናግረዋል።

“ዓመቱ በሀገሪቱ የዴሞክራሲ ተቋማት መገንባት የተቻለበት ዓመት ነበር ፤በዚህም ክልሉም ሆነ ሀገሪቱ በለውጥ ጎዳና ላይ ይገኛሉ፤ የህግ የበላይነት የበለጠ የሚጠናክሮበት ዓመት ይሆናል ብለን እንጠብቃልን” ብለዋል።

አቶ ሙስጠፌ እንዳሉት ባለፈው ዓመት መጀመሪያ አከባቢ በጅግጅጋ የነበረው ችግር ተወግዶ አሁን ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች በአንድነት በፍቅር የሚኖርበት ከተማ መሆኗንና ይሀው በቀጣይ አጠናክሮ ለማስቀጠል በትኩረት ይሰራል።

“አዲሱ ዓመት የህብረተሰቡን የልማት እና የመልካም አስተዳደር ችግሮች ለመፍታት የተያዙ እቅዶች የምንተገበርበትና ህዝቡ ያገኘውን ነፃነት የበለጠ የሚጠቀሚበት ይሆናል” ብለዋል።

የክልሉ መንግስት ሰላምና አንድነት እንዲጠናክር እንደሚሰራ አመልክተው ህዝቡም የድርሻውን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።

አቶ ሙስተፌ ሙሁመድ ለክልሉና ለሌሎችም ኢትዮጵያዊያን አዲሱ ዓመት የጤና፣ የብልጽግና የስኬት ዘመን እንዲሆን ምኞታቸውን ገልጸዋል።

ምንጭ ፦ኢዜአ