በሶማሊያ ኪስማዮ ግዛት በአንድ ሆቴል ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት በርካቶች ሞቱ

በደቡባዊ ሶማሊያ በአንድ ሆቴል ላይ በደረሰ ጥቃት ቢያንስ ሰባት ሰዎች መሞታቸው እየተነገረ ነው።

ከሟቾቹ መካከል ትውልደ ካናዳዊ የሆነችው ሶማሊያዊት የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ ሆዳን ናላህ እንደምትገኝበት ዘገባዎች ያሳያሉ።

ባለስልጣናት ከአደጋው የተረፉት ሰዎች ነገሩን በማለት እንደሚያስረዱት፤ ጥቃቱን ያደረሰው ቦንብ የጫነ የአጥፍቶ ጠፊ መኪና ወደ አሳሴይ ሆቴሉ ጥሶ ከገባ በኋላ በመፈንዳቱ ነው።

ከፍንዳታው በኋላ መሣሪያ የታጠቀ ግለሰብ ወደ ሆቴሉ በመግባት ባገኛቸው ሰዎች ላይ መተኮስ መጀመሩ ተገልጿል። አልሸባብ ለጥቃቱ ኃላፊነቱን እንደሚወስድ ገልጿል።

የአካባቢው ፖለቲከኞችና የጎሳ መሪዎች ጥቃቱ በደረሰበት ወቅት በሆቴሉ ውስጥ በቅርቡ ስለሚካሄደው የአካባቢ ምርጫ ውይይት እያደረጉ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል።

የአይን እማኞች እንደሚሉት፤ ከቦንብ ፍንዳታው በኋላ ወዲያውኑ የተኩስ እሩምታ ሰምተዋል።

ከጥቃቱ በኋላ ምናልባት ጥቃት አድራሾቹ ሊኖሩ ይችላሉ በሚል ወደ አካባቢው አንድም ብቅ ያለ አካል እንዳልነበር ለማወቅ ተችሏል።

የደህንነት አባል የሆነው አብዲ ዱሁል ለፈረንሳዩ የዜና ወኪል እንደተናገረው፤ ከሞቱት መካከል የቀድሞው የአካባቢ አስተዳዳሪ ሚኒስትር እና የሕግ አውጪው ይገኙበታል።

የአካባቢው መገናኛ ብዙኀን እና የሶማሊያ ጋዜጠኞች ማኅበር የ43 ዓመቷ ናላይህ እና ባለቤቷ ከሞቱት መካከል መሆናቸውን አረጋግጠዋል። (ምንጭ፡-ቢቢሲ)