ቻይና ለታይዋን የጦር መሳሪያ በሚያቀርቡ የአሜሪካ ኩባንያዎች ላይ ማዕቀብ እንደምትጥል አስታወቀች

ቻይና ለታይዋን የጦር መሳሪያ በሚሸጡ የአሜሪካ ኩባንያዎች ላይ ማዕቀብ እንደምትጥል አስታወቀች፡፡

የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ለታይዋን በሚፈፀመው የጦር መሳሪያ ሽያጭ ላይ በሚሳተፉ የአሜሪካ ኩባንያዎች ላይ ማዕቀብ ይጣላል ብሏል፡፡

ይህ የቻይና ውሳኔ የተሰማው አሜሪካ በ2 ነጥብ 2 ቢሊየን ዶላር ለታይዋን የጦር መሳሪያ እንደምትሸጥ ማስታወቋን ተከትሎ ነው፡፡

አሜሪካ ለታይዋን የጦር መሳሪያ ለመሸጥ ያሳለፈችው ውሳኔ አለም አቀፍ ህግን እና የአለም አቀፍ ግንኙነት መመሪያን የሚፃረር መሆኑን የሀገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጌንግ ሹዋን ተናግረዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ ቻይና ብሄራዊ ጥቅሟን ለማስጠበቅ በጦር መሳሪያ ሽያጩ ላይ በሚሳተፉ ኩባንያዎች ላይ ማዕቀብ ይጣላል ሲል አስታውቋል፡፡

የቻይና ጦር የአሜሪካ መንግስት ያሳለፈውን ውሳኔ በከፍተኛ ሁኔታ በመቃወም መግለጫ አውጥቷል፡፡

የቻይና መከላከያ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ታይዋን ከቻይና ልትለይ የማትችል አንድ አካል መሆኗን ጠቅሰው፤ ቻይና በአሜሪካ የጦር መሳሪያ ሽያጭ ላይ የያዘችው አቋም ግልፅና ቀጣይነት ያለው ነው ብለዋል፡፡

ቻይና ታይዋን የግዛቷ አንድ አካል መሆኗን ስትገልጽ፤ ታይዋን በበኩሏ ሉዓላዊ ሃገር ነኝ በማለት የቤጂንግን አካሄድ ትኮንናለች።

ከዚህ ጋር ተያይዞም ቻይና በተለይም ከአሜሪካ ጋር በተለያየ ጊዜ በታይዋን ጉዳይ ዲፕሎማሲያዊ እሰጥ አገባ ውስጥ ስትገባ ትስተዋላለች። (ምንጭ፡-አርቲ)