አምስት የአውሮፓ ሕብረት ሀገራት ስደተኞችን ሊቀበሉ ነው

አምስት የሚሆኑ የአውሮፓ ሕብረት አባል ሃገራት፤ ስፔን፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ሉክዘምበርግ እና ፖርቹጋል በጣሊያን ደሴት ላምፔሱዳ የደረሱ ስደተኞችን ሊቀበሉ መሆናቸው ተገለፀ።

ስደተኞቹን የጫነችው የእርዳታ መርከብ ተቀባይ በማጣቷ ለሳምንታት በሜዲትራኒያን ባህር ላይ ስትዋልል ቆይታ ጣሊያን ላምፔሱዳ የደረሰችው ባለፈው ማክሰኞ እንደነበር ተገልጿል።

የአገሪቷ አቃቤ ሕግ መርከቧ እንድትለቀቅ ትዕዛዝ ማስተላለፈቻውን ተከትሎ ቁጥራቸው ወደ አንድ መቶ የሚጠጉ ስደተኞችን ያሳፈረችውና 'ባለሽበት ቆይ' የተባለችው መርከብ እንድትንቀሳቀስ ተፈቅዶላታል።

ምንም እንኳን ከስደተኞቹ መካከል ህፃናትና በጠና የታመሙ ሰዎች ቢኖሩም የአገር ውስጥ ሚንስትሩ ማቴዎ ሳልቪኒ "ከዚህ በኋላ ወደቦቻችን ለስደተኞች ዝግ ናቸው።" በማለት ስደተኞቹ ከመርከቧ እንዳይወርዱ ለሦስት ሳምንታት ያህል ተከልክለው ቆይተዋል።

ቀደም ሲል 10 ስደተኞች ደሴቷ ጋር በዋና እንደርሳለን በሚል ተስፋ ከመርከቧ ዘለው ባህር ውስጥ መግባታቸው ተጠቅሷል።

በሥፍራው የሚገኙት ስደተኞችም ቆስለውና በፋሻ ተጥቅልለው ይታዩ እንደነበር ኤ ኤፍ ፒ የዜና ወኪል ዘግቧል።

ከስደተኞቹ መካከል አንዱ "ልቀውስ ትንሽ ቀርቶኝ ነበር" ሲል የነበረበትን ሁኔታ ለዜና ወኪሉ ገልጿል።

እንደ ሮይተርስ የዜና ወኪል ከሆነ የአውሮፓ ሕብረት ኮሚሽን እነዚህን ስደተኞችን የሚቀበሉ ሃገራትን ሲያፈላልግ ቆይቷል።

በመጨረሻም ስደተኞችን የጫነችው ሁለተኛዋ የእርዳታ መርከብ፤ ለ13 ቀናት በሜዲትራኒያን ባህር ላይ ከቆየች በኋላ ሃገራቱ ከአደጋው የተረፉትን ከ100 በላይ ስደተኞች ለመቀበል ፈቅደዋል ሲል ቢቢሲ ዘግቧል።