ሰላማዊ መንገድ እንዳይዘጋ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ሕወሐትን ወደ ሰላም መንገድ ሊያመጣው እንደሚገባ መንግስት አስታወቀ

ነሐሴ 20/2014 (ዋልታ) ሰላማዊ መንገድ እንዳይዘጋ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ሕወሐትን ወደ ሰላም መንገድ ሊያመጣው እንደሚገባ የኢትዮጵያ መንግስት አሳሰበ፡፡

የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በወቅታዊ ጉዳይ ላይ መግለጫ ሰጥቷል።

የመግለጫው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል:-

ያለ ጦርነት መኖር የማይችለው አሸባሪው ሕወሐት ለሰላም የተከፈቱትን በሮች ሁሉ እየዘጋቸው ነው፤ የመከላከያ ኃይላችን ይዞ በቆየባቸው ቦታዎች ላይ አሁንም ጥቃት እፈጸመ ይገኛል።

የመከላከያ ኃይላችን የመንግሥትን የሰላም አማራጭ በመያዝ በጥንቃቄ በመከላከል ላይ ነው።

እስካሁን የኢትዮጵያ መንግሥት ለሰላም ያደረጋቸው ጥረቶችና የከፈላቸው ዋጋዎች ይታወቃሉ፤ መንግሥት በሰሜን የሀገሪቱ ክፍል የተፈጠረውን ችግር በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ውሳኔ ማሳለፉ ይታወቃል ።

በዚህ ውሳኔው መሠረት የተናጠል የተኩስ አቁም አድርጓል። ለርዳታ የሚገቡ መኪኖችና ለርዳታ የሚገቡ ቁሳቁሶች ላልተገባ ተግባር መዋላቸውን እያወቀ እንኳን፣ ለሕዝቡ ሲባል፣ ወደ ትግራይ ክልል ሰብአዊ ርዳታ ያለ ችግር እንዲገባ ሁሉንም ነገር አመቻችቷል ።

የድርድር ዕቅዱንና ተደራዳሪዎቹን ይፋ አድርጓል። በማናቸውም ጊዜ፣ በማንኛውም ቦታ፣ በማናቸውም ጉዳዮች ለመነጋገር ዝግጁ መሆኑንም አሳውቋል።

ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ አሁን በግልጽ እንደታየው ሕወሐት ነዳጅ ዘራፊ ብቻ ሰይሆን ጠብ ጫሪ መሆኑን ዐውቆ ማውገዝ አለበት።

ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ፣ “ሁለቱ ወገኖች’ ከሚል ፍርደ ገምድል ጥሪ ተላቆ መንግሥት ወደ ያዘው የሰላም አማራጭ ሕወሐት እንዲመጣ ግፊት እንዲያደርግ አሁንም መንግሥት ጥሪ ያደርጋል።

ይህ ካልሆነና ሕወሐት ጥቃቱን የሚቀጥል ከሆነ፣ መንግሥት በሕግ የተጣለበትን ግዴታ ለመወጣት ሲል ማንኛውንም ርምጃ ለመውሰድ የሚገደድ መሆኑን ያሳውቃል።

ነሃሴ 20 ቀን 2014 ዓ.ም

አዲስ አበባ