በሀረሪ ክልል በ20 ሚሊየን ብር ወጪ የተከናወነ የማስፋፊያ ፕሮጀክት ተመረቀ

ግንቦት 4/2014 (ዋልታ) በሀረሪ ክልል በ20 ሚሊየን ብር የተከናወነ የትምህርት ቤት ማስፋፊያ ፕሮጀክት ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በተገኙበት በዛሬው ዕለት ተመርቋል።
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ርዕሰ መስተዳድሩ እንደተናገሩት፤ የፕሮጀክቱ መጠናቀቅ የትምህርት ተሳትፎን ከማሳደግ ባሻገር የተማሪዎች ስነ-ምግባር፣ እውቀትና ክህሎትን ከማሳደግ አንፃር የጎላ ሚና ይኖረዋል።
በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በሚከናወኑ ተግባራት ላይ ባለድርሻ አካላት ሚናቸውን እንዲያጎለብቱም ጥሪ አቅርበዋል።
የክልሉ ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዐቢይ አበበ በበኩላቸው ትምህርት ቤቱ 13 የመማሪያ ክፍሎች፣ የኮምፒዩተር ክፍል ፣ ላብራቶሪ ፣ ቤተ መጻሕፍት እና የመሰብሰቢያ አዳራሾችን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የትምህርት ቤቱን የተማሪ ቅበላ አቅም ከ860 ወደ 1 ሺሕ 200 እንደሚያሳድገውም ጠቁመዋል።
ተስፋዬ ኃይሉ (ከሀረር)