በደቡብ ክልል የተሻለ አፈጻጸም ላስመዘገቡ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ዕውቅና ተሰጠ

ጥቅምት 21/2014 (ዋልታ) የደቡብ ክልል ፍትህ ቢሮ የዜጎችን ሰብዓዊ መብት አጠባበቅና የታራሚዎችን ሰብዓዊ መብት አያያዝ ለመከታተል በወር አንድ ጊዜ ማረሚያ ቤቶችን ለመጎብኘት አቅዶ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል፡፡
በዘንድሮው በጀት ዓመት በይቅርታ አሰጣጥ አረጋዊያን፣ ታማሚዎችንና አካል ጉዳተኞችን በልዩ ሁኔታ ይቅርታ እንዲያገኙ እንደሚሠራም ተመላክቷል፡፡
በታክስ ማጭበርበር የተመዘበረ ሃብትና ንብረት የማስመለስ እና ለቀረቡ አቤቱታዎችና ጥቆማዎች የመጀመሪያ ደረጃ ውሳኔ የመስጠት እንዲሁም ተከሳሾች በሰበር የጠየቋቸው ጉዳዮች በስር ፍርድ ቤት የተሠጡ ውሳኔዎች እንዲፀኑ የማድረግ አቅም ለመፍጠር አቅጣጫ ተቀምጧል።
በሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውርና ስደተኞችን በህገ ወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀል ለመከላከል ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት መስራት እና ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ ትኩረት ተሰጥቶት እንደሚሠራም ነው የተገለጸው፡፡
በበጀት ዓመቱ ለ6 ሚሊየን 750 ሺሕ የህብረተሰብ ክፍሎች ንቃተ ሕግ ግንዛቤ ለማሳደግ እንደሚሠራም ተመላክቷል።
ጉባኤው በቀረበው እቅድ ላይ የተወያየ ሲሆን በመጨረሻም የጉራጌ ፣ የስልጤ እና የጋሞ ዞኖች እንዲሁም የደራሼ፣ የቡርጂ እና የኮንታ ልዩ ወረዳዎች የተሻለ አፈጻጸም በማስመዝገብ የዋንጫና የሴርቴፍኬት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
የተሻለ አፈጻጸም በማስመዝገብ የተሸለሙ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች እውቅናው በቀጣይ ጥንካሬያቸውን በማስቀጠል ድክመቶችን በማረም በቀጣይ የተሻለ ነገር ለመስራት እንደሚያነሳሳቸው መናገራቸውን ከጋሞ ዞን ኮሙዩኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡