ከገረገራ እስከ ጋሸና ያለው የከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር ጥገና ለማጠናቀቅ እየተሰራ ነው

ታኅሣሥ 15/2014 (ዋልታ) ከገረገራ እስከ ጋሸና ያለውን የከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር ጥገና በቀጣዮቹ አራት ቀናት ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የሰሜን ምዕራብ ሪጅን የማስተላለፊያ መስመሮችና ማከፋፈያ ጣቢያዎች ኦፕሬሽን ቢሮ አስታወቀ፡፡

የቢሮው ዳይሬክተር ውበት አቤ እንደገለፁት ከዚህ ቀደም ጉዳት ደርሶባቸው ከነበሩ የማስተላለፊያ መስመሮች በተጨማሪ አምስት ቦታዎች ላይ ጉዳት ያጋጠመ ሲሆን ሦስቱ ከባድ የመበጣጠስ ጉዳት የደረሰባቸው ነው፡፡

የደረሱትን ጉዳቶች የመጠገን ሥራ በርብርብ እየተከናወነ መሆኑን የጠቀሱት ዳይሬክተሩ በቀጣዮቹ አራት ቀናት ውስጥ ሥራው ሊጠናቀቅ ይችላል ብለዋል፡፡

በመስመሮቹ ላይ በተካሄደ የፍተሻ ሥራ በቅርቡ የደረሱትን ተጨማሪ ጉዳቶች ሳይጨምር 34  በሚሆኑ በምሰሶዎች መካከል በሚገኙ ቦታዎች ላይ 50 የመስመሮች መበጣጠስ፣ 7 የድምፅና ዳታ ማስተላለፊያ የኦፕቲካል ፋይበር መቆረጥ እና 13 ቦታዎች ላይ መስመር ሳይበጠስ ጉዳት መድረሱን ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡