ኮሚሽነር ምትኩ ካሳ ፍርድ ቤት ቀረቡ

ሐምሌ 7/2014 (ዋልታ) በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ትናንት በቁጥጥር ስር የዋሉት የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽነር ምትኩ ካሳ ፍርድ ቤት ቀረቡ፡፡

ምትኩ ካሳ እና ኢያሱ ምትኩ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ የጊዜ ቀጠሮ ችሎት ቀርበዋል።

ፖሊሰ በተጠርጣሪዎቹ ላይ እስካሁን ያሰባሰባቸውን መረጃዎች እና ማስረጃዎች ለፍርድ ቤት ማቅረቡን ኤፍቢሲ ዘግቧል፡፡

የ10 ምስክሮችን ቃል ለመቀበል እንዲሁም በፌደራል እና በክልሎች የኮሚሽኑን ቅርንጫፎች ያሉ ሰነዶች ኦዲት ለማድረግ እንዲሁም በብርበራ የተገኙ ሰነዶች እና ምንጩ ያልታወቀ የውጭ ሀገር ገንዘብን ለማጣራት እና ምርመራ ለማድረግ የ14 ቀን ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ እንዲሰጠው ፖሊስ ጠይቋል።

ተጠርጣሪዎች በጠበቆቻቸው አማካኝነት በጉዳዩ ላይ የቀድሞ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ እና ፖሊስ የምርመራ ጊዜ ከአንድ ዓመት በፊት ያለቀ በመሆኑ ለፖሊስ የጊዜ ቀጠሮ እንዳይሰጥ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል።

ግራ ቀኙን የተመለከተው ችሎቱ ለፖሊስ የ14 ቀን የምርመራ ጊዜን የፈቀደ ሲሆን ተጠርጣሪዎች ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄን ውድቅ አድርጓል።