ኮርፖሬሽኑ ከውጪ የገዛውን የአፈር ማዳበሪያ ወደ ጅቡቲ ወደብ አጓጉዞ ማጠናቀቁን ገለጸ

ሐምሌ 25/2014 (ዋልታ) የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ለ2014/15 የሰብል ዘመን ከውጪ የገዛው ከ12 ነጥብ 8 ሚሊየን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ሙሉ በሙሉ ወደ ጅቡቲ ወደብ አጓጉዞ ማጠናቀቁን አስታወቀ፡፡

የመጨረሻውን ዙር 500 ሺሕ ኩንታል ዩሪያ ማዳበሪያ የጫነች መርከብ ትላንት ጂቡቲ ወደብ መድረሷን የኮርፖሬሽኑ መረጃ አመላክቷል፡፡

ይህን ተከትሎም ኮርፖሬሽኑ ለሰብል ዘመኑ ከውጪ የገዛቸው ኤን ፒ ኤስ፣ ኤን ፒ ኤስ ቢ እና ዩሪያ የተሰኙ የአፈር ማዳበሪያዎችን ወደ ጂቡቲ ወደብ የማጓጓዙን ስራ ማጠናቀቁን ነው ያስታወቀው፡፡

ከጥር ወር ጀምሮ ወደብ ከደረሰው ማዳበሪያ ውስጥ እስከ ሐምሌ 24 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ ከ12 ሚሊየን 300 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ወይም 96 በመቶው ወደ ሀገር ውስጥ ተጓጉዞ ለአርሶ አደሩ እየቀረበ እንደሚገኝም ተጠቁሟል፡፡

ለዘንድሮ የሰብል ዘመን ኦሲፒ እና ፈርቲግሎብ ከተባሉ ዓለም አቀፍ የአፈር ማዳበሪያ አምራች ኩባንያዎች የገዛው የአፈር ማዳበሪያ የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት በመደባቸው 23 ግዙፍ መርከቦች ከሞሮኮ፣ ከዩናይትድ አረብ ኤምሬትስና ከግብጽ ተጓጉዞ መጠናቀቁ ተገልጿል፡፡

ኮርፖሬሽኑ የግብርና ሚኒስቴር በየዓመቱ አጥንቶ በሚያቀርበው ሀገራዊ የአፈር ማዳበሪያ ፍላጎት መሰረት ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ ማዳበሪያ ከውጪ እየገዛ የሚያቀርብ መንግሥታዊ የልማት ድርጅት ነው።