የሳምቤ ታሪክ ኦሮሞ በኢትዮጵያ ግንባታ ውስጥ የነበረውን ታሪክ የሚያሳይ 2ኛው አድዋ ነው

ሚያዝያ 26/2014 (ዋልታ) የሳምቤ ታሪክ ኦሮሞ በኢትዮጵያ ግንባታ ውስጥ የነበረውን ታሪክ የሚያሳይ ነገር ግን ያልተነገረለት ሁለተኛው አድዋ ነው ሲሉ የኦሮሚያ ባህል እና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ሰዓዳ ኡስማን ገለጹ።

የሳምቤ ድል የኦሮሞ አርበኞች ዘመናዊ የጦር መሳሪያን ከታጠቀው የጣሊያን ወራሪ በአድዋ ጦርነት የደረሰበትን ሽንፈት ለመበቀል ሲል ወደ ኢትዮጵያ ጦሩን ልኮ ከባድ ውጊያ ካካሄደባቸው የአገሯቷ ክፍሎች ውስጥ በዋናነት የሚጠቀስ ነው፡፡

በኢሉ ኣባ ቦራ ዞን ጎሬ ከተማ በሚገኘው በዚህ ስፍራ ላይ የኦሮሞ ጀግኖች ከተማዋን ለመውረር የመጣውን ፋሽስት ከባድ ተጋድሎን በማድረግ ከተማዋን ታድገዋል።

በ1928 ዓ.ም የኢትዮጵያ ዋና ከተማ የነበረችው ጎሬ የኢትዮጵያ ንጉስ የነበሩት ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ሚኒስትሮቻቸውን በመሰብሰብ ከተማዋን በዋና መዲናነት መሰየማቸው ይነገራል።

ይህም ለሰባት ወራት ያክል በመዲናነት አገሪቷን ያገለገለች ስትሆን በከተማዋም ውስጥ የእንግሊዝ ቆንፅላ ተከፍቶ አገልግሎት ሲሰጥ እንደነበር መረጃው ያወሳል።

የፋሺስቱ ቡድን ይህችን ከተማ ለመቆጣጠር በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ በ1933 ዓ.ም በሳምቤ ተራራ ላይ ውጊያ ቢከፍትም ከ1ሺሕ 500 በላይ ኃይሉ እና ከ20 ሺሕ በላይ መሳሪያን አስማርኮ ሊሸነፍ ችሏል።

ይህ ታሪክ ለዘመናት ታፍኖ መቆየቱን የገለፁት የቢሮው ኃላፊ ሰዓዳ ኡስማን የኦሮሞ ሕዝብ በኢትዮጵያ ታሪክ ባንዳ ሳይሆን ለዛሬዋ ኢትዮጵያ የነበረውን ድርሻ የሚያሳይ ነው ብለዋል።

ለ78 ዓመታት የኢሉ አባ ቦራ ዋና ከተማ የነበረችው ጎሬ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ከመሆኗም በተጨማሪ የኢትዮ-ሱዳን የንግድ ማዕከልም ነበረች።

ይህንን ተከትሎም እንደ ዲንሾ እና የሙሴ ድልድይ የተሰኙ ትላልቅ ቁጥራቸው ሰባት የሚሆኑ ኩባንያዎች መቀመጫም ነበረች።

ከዚህም በተጨማሪ የክርስትና ሃይማኖት መስፋፋት ተከትሎ መፅሐፍ ቅዱስ በኦሮምኛ በመተርጎም ለዓለም ያበረከተው ኦኖስሞስ ነሲብም በዚሁ አካባቢ ይገኛል።

ይህንን ታሪክ በማበልፀግ እና በመጠበቅ ለቀጣይ ትውልድ እንዲተላለፍ ከማድረግም በተጨማሪ የአካባቢውን ታሪካዊ እና ተፈጥሯዊ መስህቦችን ወደ ሀብት ለመቀየር የሚመለከታቸው አካላት ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።

በጎሬ ከተማ የመላው አፍሪካዊያን ኩራት የሆነው የነጮች የበላይነት የወደቀበት የሳምቤ ድል ቀን በጎሬ ከተማ እየተከበረ ይገኛል።

ሚልኪያስ አዱኛ (ከጎሬ)