የአቪዬሸን አሰራርን ጥሰዋል በተባሉ 6 ተጠርጣሪዎች ላይ የሽብር ወንጀል ምርመራ ተጀመረ

ነሐሴ 19/2016 (አዲስ ዋልታ) ፌደራል ፖሊስ ሰሞኑን ከአዲስ አበባ መቀሌ ለጉዞ በተዘጋጀ አውሮፕላን ውስጥ የአቪዬሸን አሰራርን በጣሰ መንገድ ግርግርና ወከባ በፈጠሩ 6 ተጠርጣሪዎች ላይ የሽብር ወንጀል ምርመራ መጀመሩን አስታወቀ።

ተጠርጣሪዎቹ ዮሀንስ ዳንኤል በርሄ፣ አማኑኤል መውጫ አብርሃ፣ ናትናኤል ወንድወሰን ሹሜ፣ ኤልያስ ድሪባ በዳኔ፣ ይዲድያ ነጻነት አበበ እና እሌኒ ክንፈ ተክለአብ ናቸው።

የፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ የምርመራ መዝገብ እንደሚያሳየው እነዚህ ተጠርጣሪዎች ተፈጥሮ በነበረው የአየር መዛባት ምክንያት አውሮፕላኑ መብረር አይችልም እየተባለ አስገድዶ ለማስኬድ የፈጠሩት አምባጓሮ በወንጀል ሕጉ ተጠያቂ ያደርጋቸዋል ብሏል።

የፖሊስ የምርመራ ቡድን ተጠርጣሪዎች ላይ በወንጀል ተጠያቂ ለማድረግ ከተጀመረው ምርመራ ባሻገር፣ ከጸረሰላም ኃይሎች ተልእኮ ተቀብለው የተንቀሳቀሱ በመሆናቸው በሽብር ወንጀልም መጠርጠራቸውን ነው የሚያመላክተው።

በወቅቱ የአየር መንገዱ ከደህንነት ኃይሎች ጋር በመሆን በትዕግስት ቢማጸናቸውም ድብቅ አጀንዳቸውን እያራመዱ በመሆናቸው አሻፈረን ማለታቸውንም በምርመራ መዝገቡ ማካተቱን የኢቢሲ ዘገባ ያመላክታል።

ማህበራዊ ሚዲያን ለበጎ ተግባር መጠቀም ሲገባቸው የሀገር ኩራት እና የራሳቸው ንብረት የሆነውን አየር መንገድ ማንቋሸሻቸው አሳዛኝ ተግባር ስለመሆኑም የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ ገልጿል።

በመሆኑም እነዚህ በቁጥጥር ስር የሚገኙ 6 ተጠርጣሪዎችን ቢሮው በተላለፉት የሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ የበረራ አሰራር ጥሰት ብሎም በሽብር ወንጀሎች የምርመራ መዝገብ ነገ ነሐሴ 20/2016 ፍርድ ቤት እንደሚያቀርባቸው ለማወቅ ተችሏል።