የፓሪስ 2024 ኦሎምፒክ የኢትዮጵያን ቱሪዝም ለዓለም የምናስተዋወቅበት መድረክ ይሆናል- አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ

ሐምሌ 17/2016 (አዲስ ዋልታ) የፓሪስ 2024 ኦሎምፒክ የኢትዮጵያን ቱሪዝም ለዓለም የምናስተዋወቅበት መድረክ ይሆናል ሲሉ የቱሪዝም ሚኒስትር አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ ገለጹ፡፡

የቱሪዝም ሚንስቴር በፓሪስ ኦሎምፒክ ለሚሳተፉ አትሌቶች የሽኝት መርሀ ግብር አድርጓል::

አርብ የሚጀመረውን የፓሪስ ኦሎምፒክ 1 ነጥብ 5 ቢሊየን የዓለም ህዝብ በቴሌቪዥን መስኮት እንዲሁም ከ8 ሚልዮን በላይ ህዝብ በአካል በመገኘት እንደሚመለከተው ይጠበቃል::

በዚህ ትልቅ ዓለም አቀፍ መድረክ የኢትዮጵያን ምድረ ቀደምትነት እና ያሉንን የቱሪዝም ሀብቶች ከመክፈቻው እለት ጀምሮ  አትሌቶቻችን በሚሳተፉባቸው በሁሉም ውድድሮች የማስተዋወቅ ስራ እንደሚሰራ አምባሳደር ናሲሴ ተናግረዋል::

ለዚህም የሚሆን የተለያዩ የህትመት ስራዎች እና አልባሳት በቱሪዝም ሚኒስቴር አማካኝነት መዘጋጀታቸውንም ጠቅሰዋል::

አትሌቶቻችን በሚያደርጓቸው ውድድሮች ካሸነፉ በኋላ ለ1 ደቂቃ ያህል በስታዲየሙ ውስጥ የሚከፈት የኢትዮጵያን ምድረ-ቀደምትነት የሚገልፅ ሙዚቃ እና ምስልም ይፋ ሆኗል::

አምባሳደር ናሲሴ አትሌቶች፣ የኦሎምፒክ ኮሚቴ እና አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በፓሪስ ኦሎምፒክ  የኢትዮጵያን ቱሪዝም ለማስተዋወቅ ሚኒስቴሩ ያቀረበላቸውን ጥያቄ ተቀብለው ለሚያደርጉት አስተዋጽዖ ምስጋና አቅርበዋል::

 

በለዊ በለጠ