ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ኢትዮጵያን ለዓለም ማሳየት ያለብን ከአድዋ ከያዝነው እሴት ጋር አያይዘን ሊሆን እንደሚገባ አሳሰቡ

የካቲት 23/2014 (ዋልታ) ኢትዮጵያን ለዓለም ማሳየት ያለብን ከአድዋ ከያዝነው እሴት ጋር አያይዘን እንጂ በመከፋፈል አይደለም ሲሉ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ገለጹ፡፡

እንደአገር ለማደግ መሠረትን ማጠናከር እና ታሪክ ላይ የጋራ መግባባት መያዝ እንደሚያስፈልግም አሳስበዋል።

የኦሮሚያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አወል አብዲ በበኩላቸው የአድዋ ድል መላ ኢትዮጵያዊያን በጋራ ሆነው የጣሊያን ወራሪ ኃይል አሳፍረው የመለሱበት እለት ነው ብለዋል፡፡

የአሁኑ ትውልድም የቀደምት አባቶቹን የአሸናፊነት መንፈስ በመውረስ አገር ሊያፈርስ የተነሳውን የሕወሓት የሽብር ቡድንን ድል በመንሳት የአገር አንድነት ማስጠበቁንም መጥቀሳቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

የዓድዋ ድል በህዳሴ ግድብ ይደገማል ሲሉ የታላቁ የኢትዮጵያ ኅዳሴ ግድብ ብሔራዊ ማስተባበሪያ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር አረጋዊ በርሄ መናገራቸውን የኢብኮ ዘገባ አመላክቷል፡፡

በዓድዋ ወራሪውን ጦር በጋራ ክንዳችንን መክተን እንደመለስነው ሁሉ፣ ክንዳችንንን አስተባብረን አገራችንን ለማልማት እና ለማበልጸግ ቆርጠን መነሳት አለብንም ብለዋል።