ኢህአዴግ ዶክተር አብይን ሊቀመንበር፤ አቶ ደመቀን ምክትል አድርጎ መረጠ

11ኛው የኢህአዴግ ጉባኤ  ዶክተር አብይ አህመድን የኢህአዴግ ሊቀመንበር ፣ አቶ ደመቀ መኮንን  ምክትል ሊቀመንበር አድርጎ  መረጠ ።  

በሐዋሳ  ከተማ ለሦስተኛ ቀን እየተካሄደ ባለው  የ11ኛው  የኢህአዴግ ጉባኤ  የድርጅቱን  የሊቀመንበርና ምክትል  ሊቀመንበር ለመምረጥ  ድምጽ  የመሥጠት  ሥነ -ሥርዓት ተካሄዶ   ዶክተር አብይ  አህመድና  አቶ ደመቀ  መኮንን በሊቀመንበርነትና በምክትል ሊቀመንበርነት በድጋሚ  ተመርጠዋል  ።

ኢህአዴግ  በዛሬው ዕለት ባካሄደው  የአመራር ምርጫ  ዶክተር አብይ አህመድ፣ አቶ ደመቀ መኮንንና ዶክተር  ደብረጽዮን ገብረሚካኤልን በእጩነት  ያቀረበ ሲሆን  ሶስቱም ለኢህአዴግ ለሊቀመንበርና ምክትል ሊቀመንበርነት ተወዳድረዋል ።  

የድርጅቱን  መሪዎች ለመምረጥ  በአጠቃላይ  177 ሰዎች  ድምጽ  እንዲሠጡ የተደረገ ሲሆን    ዶክተር አብይ አህመድ  176 ድምጽ  በማግኘት  ነው  ለቀጣይ  ዓመታት  የኢህአዴግ  ሊቀመንበር ሆነው  እንዲያገለግሉ  የተመረጡት ።

ለኢህአዴግ ምክትል ሊቀመንበርነት በተሠጠው ድምጽ  አቶ ደመቀ መኮንን  አጠቃላይ ከተሠጠው  ድምጽ የ149 ሰዎች ድምጽን  በማግኘት ነው  የኢህአዴግ  ምክትል ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ።

ሌላው  ተወዳዳሪ ዶክተር ደብረጽዮን ገብረ ሚካኤል ለድርጅቱ  አመራርነት በተሠጠው በአጠቃላይ 15 ድምጽ  አግኝተዋል  ።