2ኛው የዓለም አቀፍ የፖስታ ህብረት ኮንግረስ ልዩ ስብሰባ እየተካሄደ ነው

2ኛው የዓለም አቀፍ የፖስታ አገልግሎት ህብረት ኮንግረስ ልዩ ስብሰባ  በዛሬው ዕለት በአፍሪካ  ህብረት  አዳራሽ እየተካሄደ ነው ።

የፖስታ ህብረት ኮንግረስ ልዩ ስብሰባው ከዛሬው ጀምሮ  ለአምስት ቀናት  ያህል  የሚካሄድ  መሆኑ ተገልጿል  ።

ከ118  ዓመት በኋላ የዓለም አቀፍ የፖስታ አገልግሎት ህብረት ኮንግረስ በዛሬው  ዕለት መካሄድ በተጀመረው  ልዩ ስብሰባው የዓለም አቀፍ የፖስታ አገልግሎት ህብረት  ጀነራል ዳይሬክተር በሽር አብዱራሂም ፣ ፕሬዚደንት ሙላቱ ና  የኢፌዴሪ የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ሚንስትር ወይዘሮ ኡባ መሐመድ ተገኝተዋል ።  

ፕሬዚደንት  ሙላቱ  በስብሰባው መክፈቻ  ላይ ንግግር ያደረጉ ሲሆን  ጉባኤው  በኢትዮጵያ  በመካሄዱ ደስተኛ መሆናቸውንና  የፖስታ አገልግሎትን ዘመናዊ  በማድረግ ለዘላቂ ልማት  የሚያበከክተውን  አስተዋጽኦ  ለማሳደግ እየተሠራ ነው  ብለዋል ።

የፖስታ አገልግሎቱን ዓለም አቀፍ  አስተዋጽኦ ከፍ ለማድረግም  በውይይቱ የሚሳተፉ  የውሳኔ ሰጪዎች ሚናቸውን እንዲወጡ አደራ  እላለው ብለዋል ።

የዓለም አቀፉ  የፖስታ  አገልግሎት ህብረት  ጄነራል ዳይሬክተር  በሽር አብዱራሂም  በበኩላቸው  በዓለም አቀፍ  ደረጃ  የፖስታ  አገልግሎትን ለማሳደግና አሠራሩን  ዘመናዊ ለማድረግ  የሚያስችሉ የውይይት ነጥቦች  ይነሳሉ  ብለዋል ።

2ኛው ዓለም አቀፍ የፖስታ  አገልግሎት  ህብረት ኮንግረስ  ልዩ ስብሰባም ስኬታማ  እንዲሆን  የኢትዮጵያ መንግሥት  ላደረገው  አስተዋጽኦም  ምስጋና  አቅርበዋል  ።

የመገናኛና ኢንፎርሜሽን  ሚኒስትር ወይዘሮ ኡባ መሓመድ  በበኩላቸው  ዛሬ  የተጀመረው ጉባኤው የፖስታ  አገልግሎቱን  ህልውና ለማስቀጠል  ትኩረት  በሚሠጥበት  ጊዜ  መካሄዱ  ልዩ ያደርገዋል ።

የፖስታ  አገልግሎቱን በኢንፎርሜሽን  ቴክኖሎጂ  በመታገዝ ዘመናዊ የማድረግም ሥራዎችም   እየተከናወኑ  እንደሚገኝም   ወይዘሮ ኡባ አያይዘው  ገልጸዋል ።

የዓለም አቀፍ የፖስታ አገልግሎት ህብረት በአጠቃላይ 192 ያህል አባል አገራትን ያካተተ ሲሆን  የመጀመሪያው  ጉባኤው  እኤአ በ1900 ነው የተካሄደው ።