የአፍሪካ ሀገራት የበጀታቸውን ዘጠኝ በመቶ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ያውላሉ

የአፍሪካ ሀገራት የበጀታቸውን ዘጠኝ በመቶ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እንደሚያውሉ የዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት አስታወቀ፡፡

ድርጅቱ ባወጣው ሪፖርት እንደገለጸው ከሌሎች አህጉራት አንጻር አፍሪካ የምትለቀው ሙቀትን የሚጨምሩ ጋዞች (Greenhouse gases) መጠን ዝቅተኛ ነው። ይሁን እንጂ የሙቀት መጠኗ ከዓለም አማካይ መጠን በላይ እየጨመረ ነው ብሏል፡፡

የአፍሪካ ሀገራት አሁን ላይ ከ2 እስከ 5 በመቶ የነፍስ ወከፍ ገቢያቸውን በከፍተኛ የሙቀት መጨመር፣ በከባድ ዝናብ፣ በጎርፍ፣ በአውሎ ነፋሶች እና የተራዘሙ ድርቆች ምክንያት ያጣሉ።

በመጪው 10 ዓመታት ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ ሀገራት ከሚቀያየረው የአየር ንብረት ጋር ተስማምቶ ለመኖር በዓመት ከ30 እስከ 50 ቢሊየን ዶላር ወጪ ያስወጣቸዋል። በመሆኑም ሀገራት በውሃና ሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ላይ ኢንቨስት ማድረግ እንዳለባቸው ሪፖርቱ ጠቅሷል።

በቅድመ ጥንቃቄ እርምጃዎችም ላይ በደንብ በመስራት ህይወት ማዳን እንዳለባቸው ተገልጿል።

በ2030 1 መቶ የሞሆነው ወይም 18 ሚሊዮን የሚደርሱ በአህጉሪቷ የሚገኙ ደሀ ዜጎች በአየር ንብረት ምክንያት ለድርቅ፣ ለጎርፍና ለከፍተኛ ሙቀት ተጋላጭ ይሆናሉ። ይህም አህጉሪቷ ድህነትን ለመቀነስ የምታደርገወን ጉዞ ወደኋላ የሚያስቀር መሆኑ ተጠቅሷል።

አፍሪካ ውስጥ የበረዶ ግግር ያለባቸው ማውንት፣ ኬኒያ ሩዌንዞሪ እና የኪሊማንጃሮ ተራራዎች ሲሆኑ ያለባቸው የበረዶ ግግሮች ግን በ2040 ሙሉ በሙሉ እንደሚቀልጡ የዓለም ሚቲዎሮሎጂ ደርጅት መረጃ ያሳያል፡፡ ይህም የመሬትን ስርዓት በእጅጉ እንደሚቀይረው የደርጅቱ ዋና ጸሐፊ ይገልጻሉ።

በቅርብ ዓመታት የአፍሪካ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥን ለመዋጋት የተሻለ የገንዘብ ድጋፍ እያገኙ ቢሆንም ከዓመቱ ለአየር ንብረት ለውጥ ለመዋጋት ከሚውለው የገንዘብ ድጋፍ ግን ከአንድ  በመቶ በታች  ያገኛሉ።

በመሆኑም ሀገራቱ በመጪው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ጉባዔ ላይ  የተሻለ የገንዘብ ድጋፍ እንዲያገኙ ማድረግ እንዳለባቸው በሪፖርቱ መገለጹን ሮይተርስ ዘግቧል።