ሁለት ህፃናትን በአሰቃቂ ሁኔታ ህይወታቸው እንዲያልፍ አድርጋለች በተባለችው ግለሰብ ላይ የጥፋተኝነት ፍርድ ተሰጠ

ኅዳር 13/2015 (ዋልታ) ሁለት ህፃናትን በአሰቃቂ ሁኔታ ህይወታቸው እንዲያልፍ አድርጋለች በተባለችው ሕይወት መኮንን ላይ የጥፋተኝነት ፍርድ ተሰጠ።

በፍትህ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ዘርፍ በሴቶች እና ህጻናት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀል ጉዳዮች ዐቃቤ ህግ ዳይሬክቶሬት ነሐሴ 26 ቀን 2014 ዓ.ም በለሚኩራ ክ/ከተማ አራብሳ ኮንዶሚኒዬም እየተባለ በሚጠራው አካባቢ በቤት ሰራተኛነት ተቀጥራ በምትሰራበት መኖሪያ ቤት ውስጥ ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ የሁለት ህጻናትን ሕይወት በአሰቃቂ ሁኔታ እንዲያልፍ አድርጋለች ሲል በከባድ የግድያ ወንጀል እንዲሁም ተከሳሽ የሟቾችን የቤተሰብ ሰነድ ማስረጃዎች ማጥፋት ወንጀል ጥቅምት 15 ቀን 2015 ዓ.ም በህይወት መኮንን ላይ ተደራራቢ ክስ መስርቶባት ተከሳሽ ወንጀሉን አልፈጸምኩም በማለት ክዳ የተከራከረች በመሆኑ ዐቃቤ ሕግ ተከሳሽ ወንጀሉን መፈጸሟን ያስረዳሉ ያላቸውን 7 የሰው ምስክሮችን አቅርቦ ለችሎቱ ማሰማቱን፤ ችሎቱም መርምሮ በጉዳዩ ላይ ብይን ለመስጠት ለኅዳር 13 ቀን 2015 ዓ.ም ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

በዛሬው ዕለት ጉዳዩን የተመለከተው የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ ሰው ግድያና ከባድ ውንብድና ወንጀል ችሎት ተከሳሽ በተከሰሰችባቸው ተደራራቢ ክሶች እንድትከላከል በማለት ብይን ቢሰጥም የመከላከያ ማስረጃ የለኝም በማለት የገለፀች በመሆኑና የመከላከል መብቷ ታልፎ ፍርድ ቤቱ ዐቃቤ ሕግ ክሱን በማስረጃ ያረጋገጠ በመሆኑ ተከሳሽን ጥፋተኛ በማለት ፍርድ ሰጥቷል፡፡

ፍርድ ቤቱም ቅጣት ለመወሰን ለኅዳር 26 ቀን 2015 ዓ.ም ቀጠሮ መስጠቱን ከሚኒስቴሩ ማኅበራዊ ትስስር ገጽ ያገኘነው መረጃ አመላክቷል፡፡