“ህወሓት” እና ‘’ሸኔ’’ በሽብርተኝነት እንዲሰየሙ የቀረበውን የውሳኔ ሀሳብ ለመቃወም የሚያስችል ማስረጃ ያለው ማንኛውም ግለሰብ እንዲያቀርብ ጥሪ ቀረበ

“ህወሓት” እና ‘’ሸኔ’’

ሚያዝያ 25/2013 (ዋልታ) – የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት “ህወሃት” እና ‘’ሸኔ’’ በሽብርተኝነት እንዲሰየሙ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የቀረበውን የውሳኔ ሀሳብ ለመቃወም የሚያስችል ማስረጃ ያለው ማንኛውም ግለሰብ በ48 ሰአታት ውስጥ በአካል እንዲያቀርብ ጥሪ አቀረበ።

ምክር ቤቱ በአዋጁ አንቀጽ 21 ንኡስ አንቀጽ 1 በተደነገገው መሠረት “ህወሃት” እና ‘’ሸኔ’’ ላይ የቀረበውን የውሳኔ ሀሳብ ለመቃወም የሚያስችል ማንኛውም ማስረጃ ካላቸው ማስታወቂያው በመገናኛ ብዙሃን ከተነገረበት ሰዓት ጀምሮ ባሉት 48 ሰዓታት ውስጥ በምክር ቤቱ ጽ/ቤት በአካል በመገኘት እንዲያቀርቡ ጥሪ አቅርቧል።

የሽብር ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በወጣው አዋጅ ቁጥር 1176/2012 አንቀጽ 2 ንኡስ አንቀጽ 2 መሠረት የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሚያዚያ 23 ቀን 2013 ዓ/ም ባካሄደው 23ኛ አስቸኳይ ስብሰባ ህዝበ ወያኔ ሓርነት ትግራይ /ህወሓት/ እና ‘’ሸኔ’’ ድርጅቶች በሽብርተኝነት እንዲሰየሙ የውሳኔ ሃሳብ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማቅረቡንም ከምክር ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡