ለሕክምና ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት የጤና አገልግሎትን በቀላሉ ማድረስ የሚያስችል የጥሪ ማዕከል ይፋ ሆነ

ሐምሌ 20/2013(ዋልታ) – ለተለያዩ የሕክምና ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት የጤና አገልግሎትን ለኅብረተሰቡ በቀላሉ ማድረስ የሚያስችል የጥሪ ማዕከል ይፋ ሆነ። አገልግሎቱ በ’ቴሌ ብር’ እና በ’ሄሎ ጤና’ ትብብር የሚሰጥ ነው።

የሕክምና ባለሙያዎች ምላሽ የሚሰጡበትን የጥሪ ማዕከል አገልግሎቱን ለማግኘት በቴሌ ብር በኩል የአገልግሎት ክፍያ መፈፀም እንደሚያስፈልግ ተገልጿል።

የኢትዮ-ቴሌኮም የሞባይል መኒ የስራ ክፍል ኃላፊ አቶ ብሩክ አድሃና እንደገለጹት ቴሌኮሙ ኅብረተሰቡን የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ለማድረግ እየሰራ ነው።

አገሪቷ ወደ ዲጂታል ኢኮኖሚ እየተጓዘች መሆኗንና ኢትዮ ቴሌኮም በዋናነት በቴሌብር በኩል ይህንኑ እያገዘ እንደሆነ ገልጸዋል።

የጤናውን ዘርፍ ለማገዝ የሕክምና አገልግሎት ከምክር ጋር ማግኘት የሚያስችል 8455 የጥሪ ማዕከል ለሚሰጠው አገልግሎት ኅብረተሰቡ ክፍያውን ከቴሌ ብር ዋሌት መክፈል እንዲችል ተደርጓል ብለዋል።

የሄሎ ጤና ዋና ስራ አስኪያጅ ዶክተር ሜሎን በቀለ በበኩላቸው ‘ሄሎ ጤና’ የተሰኘው አገልግሎት ኅብረተሰቡ በማንኛውም ቦታና ሠዓት የምክር አገልግሎትና የሕክምና ቀጠሮ ማመቻቸት እንደሚያስችል አስረድተዋል።

የጥሪ ማዕከሉ 24 ሠዓት አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ተላላፊ በሆኑና ባልሆኑ በሽታዎች እንዲሁም ኮቪድ-19ን ለተመለከቱ ጥያቄዎች በሕክምና ባለሙያዎች ምላሽ መስጠት የሚያስችል ነው ብለዋል።

አገልግሎቱ የሕክምና ማዕከላትን መጨናነቅ ለመቀነስ፣ ታካሚዎች ከአገር ውስጥ በተጨማሪ በውጭ አገራትም ቀጠሮ ለማስያዝም እንዲሁ።

አገልግሎቱ በአማርኛ፣ በኦሮምኛና በሶማሊኛ ቋንቋዎች እንደሚሰጥና በቀጣይ ሌሎች የአገር ውስጥና የውጭ ቋንቋዎች እንደሚካተቱ መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

በጥሪ ማዕከሉ የእንስሳትና የእፅዋት ሕክምና የማማከር አገልግሎት በተጨማሪ እንደሚሰጥ አክለዋል።

ኢትዮ-ቴሌኮም ከቴሌ ብር ጋር መስራት ለሚሹ አጋር ድርጅቶች በሩ ክፍት መሆኑን አስታውቋል።