በህዳር ወር ከ19 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ ተሰበሰበ- የገቢዎች ሚኒስቴር

በህዳር ወር 19 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡን የገቢዎች ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

ገቢው ከሃገር ውስጥ፣ ከወጪ ንግድ ቀረጥና ታክስ እንዲሁም ከሎተሪ ሽያጭ 19 ቢሊየን 224 ሚሊየን 974 ሺህ 139 ብር በመሰብሰብ የዕቅዱን 92 በመቶ ማሳካቱን ገልጿል፡፡

ከህዳር ወር አፈፃጸም ውስጥ 9 ቢሊየን 892 ሚሊየን 322 ሺህ 712 ብር ከሃገር ውስጥ ገቢ የተሰበሰበ ሲሆን 9 ቢሊየን 306 ሚሊየን 966 ሺህ 923 ብር ደግሞ ከወጪ ንግድ ቀረጥና ታክስ ቀሪው ከሎተሪ ሽያጭ የተሰበሰበ መሆኑ ተመላክቷል።

በያዝነው በጀት ዓመት ከሐምሌ እስከ ህዳር ባሉት አምስት ወራት ብቻ 126 ቢሊየን 835 ሚሊየን 480 ሺህ 740 ነጥብ 99 ብር በመሰብሰብ 101 በመቶ አፈፃጸም ተመዝግቧል፡፡

ከዚህ ባለፈም አፈፃፀሙ ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከ17 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር በላይ ጭማሪ አሳይቷል፡፡

የገቢ ዓይነቶች ድርሻ ሲታይ ከሃገር ውስጥ ገቢ 80 ነጥብ 96 ቢሊየን ብር፣ ከወጪ ንግድ ቀረጥና ታክስ 45 ነጥብ 77 ቢሊየን ብር እና ከሎተሪ ሽያጭ 109 ነጥብ 45 ሚሊየን ብር ነው የተሰበሰበው፡፡

በ2013 በጀት ዓመት 290 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ እየተሰራ ሲሆን እስካሁን ባለው አፈፃፀምም 126 ነጥብ 85 ቢሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡን ከገቢዎች ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።