በደቡብ ክልል በበልግ እርሻ 400 ሺሕ ሄክታር መሬት በዘር ተሸፍኗል

ግንቦት 4/2014 (ዋልታ) በደቡብ ክልል እየተካሄደ ባለው የበልግ እርሻ እንቅስቃሴ እሰካሁን በተደረገው እንቅስቃሴ 400 ሺሕ ሄክታር መሬት በዘር መሸፈኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።
የቢሮው ምክትል ኃላፊ ዳንኤል ዳምጠው እንደገለጹት በዘር የተሸፈነው መሬት በክልሉ በ2014/2015 ምርት ዘመን በተለያየ ሰብል ለማልማት ከታቀደው አንድ ሚሊዮን ሄክታር ውስጥ ነው።
የዘንድሮ በልግ ዘናብ ዘግይቶ በመግባቱና የዝናብ መቆራረጥ ችግር በማጋጠሙ ምክንያት በአብዛኞቹ በልግ አብቃይ በሆኑ አካባቢዎች የበልግ እርሻው ዘግይቶ መጀመሩን ተናግረዋል።
የዝናብ ሥርጭቱ መሻሻል እያሳየ ከመጣ እስከ ግንቦት ወር መጨረሻ ድረስ ዕቅዱን ለማሳካት ርብርብ እንደሚደረግ አስታውቀዋል።
በበልግ ልማቱ ከ2 ሚሊዮን በላይ አርሶና ከፊል አርብቶ አደሮች፣ ወጣቶችና ሴቶች በመሳተፍ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የበልግ ልማቱን ዕቅድ ለማሳካት 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ለማቅረብ ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በክልሉ የሚመረቱት ዋና ዋና ሰብሎች ለሀገር ውስጥ የምግብ ፍጆታ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለውጭ ገበያ ካላቸው አገልግሎት አንጻር መለየታቸውን አስረድተዋል።
በምርት ዘመኑ ከሚለሙት መካከል በቆሎ፣ ማሽላ፣ ቦሎቄ፣ ድንችና ስኳር ድንች በዋነኝነት እንደሚገኙበት ጠቅሰው፣ በነዚህ ስፔሻላይዝ ለማድረግ መታቀዱን ተናግረዋል።
በበልግ ወቅት ከሚለማው መሬት 85 ሚሊዮን ኩንታል የአገዳ፣ የጥራ ጥሬና የቅባት እህሎች እንዲሁም የስራ ስር ምርት እንደሚገኝ ይጠበቃል ብለዋል።
”ዘንድሮ በተወሰነ ደረጃ የበቆሎ ምርጥ ዘር እጥረት አጋጥሞናል” ያሉት ምክትል ኃላፊው ሆኖም በስራ ስር ዘሮች በመተካት የማቻቻል ተግባር መከናወኑን ተናግረዋል።
እንደኢዜአ ዘገባ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በበልግ የምርት ዘመን ከሚለው ሰብል 75 በመቶ በኩታ ገጠም የአስተራረስ ሥርዓት እየተመራ መሆኑን አስታውቀዋል።