አሞሌ የአመቱን ዓለምአቀፍ ከፍተኛ ተፅዕኖ ፈጣሪ ዲጂታል ዋሌት ሽልማት አሸነፈ

ዳሽን ባንክ ከ2010 ዓ.ም ጀምሮ ከሞኔታ ቴክኖሎጂ አ.ማ ጋር በመተባበር አሞሌ የተሰኘውን ዘመናዊ የክፍያ፣ ገንዘብ የማስተላለፍና ግብይት የማስፈፀም አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

አሞሌ የተለያዩ ግዙፍ ተቋማት ክፍያ በቀላሉ እንዲሰበስቡና እንዲፈፅሙ በማስቻሉ ተመራጭነቱ እየጨመረ ይገኛል፡፡

አሁን ላይም በአሞሌ አማካኝነት በወር በአማካኝ ከ200 ሚሊየን ብር በላይ ልውውጥ እየተደረገበት ሲሆን÷አሞሌ በአሁኑ ወቅት ከ3 ሚሊየን በላይ ደንበኞች እንዳሉትም ባንኩ ለዋልታ የላከው መግለጫ ያመላክታል።

አሞሌ በሃገሪቱ የዲጂታል ኢኮኖሚን ለማስፋፋት የበኩሉን አስተዋፅኦ እያበረከተ ሲሆን÷ ከገንዘብ ንክኪ ነፃ የሆነ ግብይትን በቀላሉ ለማከናወን ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩ ተመራጭ መሆኑም ተመላክቷል።

በተጨማሪም ተመራጭነቱ ከሃገር ዉስጥ አልፎ ዓለምአቀፍ ዕውቅና ለማግኘት አስችሎታል፡፡

በዚህም በእንግሊዝ የሚገኘውና በዓለም አቀፍ የባንክና ፋይናንስ ኢንዱስትሪ ላይ የተለያዩ ጥናቶችን የሚያከናውነዉውና ሽልማት የሚሰጠው አይ ቢ ኤስ ኢንተለጀንስ የተሰኘ ተቋም ዳሸን ባንክ በአሞሌ ዋሌት አማካኝነት የ2020 የአመቱ ከፍተኛ ተፅዕኖ ፈጣሪ የዲጂታል ዋሌት ዘርፍ ሽልማት ማሸነፉን ይፋ አድርጓል፡፡

አሞሌ ይፋ በተደረገ በሁለት አመት ጊዜ ዉስጥ ከሶስት ሚሊየን በላይ ሰዎች አካውንት ከፍተው እየተጠቀሙበት መሆኑንም መረጃው ያመላክታል፡፡