አቶ  ደመቀ መኮንን በኢትዮጵያ የዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ኮሚቴ የሚስዮኑ ኃላፊ ጋር ተወያዩ

አቶ  ደመቀ መኮንን

ግንቦት 04/2013 (ዋልታ) – ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በኢትዮጵያ የዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ኮሚቴ የሚስዮን ኃላፊ  የሆኑትን ፊሊፕ  ቦቨርዲን  በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።

አቶ ደመቀ የዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ድርጅት በኢትዮጵያ በሚፈጠሩ ሰው ሰራሽ ግጭቶች እንዲሁም እንደ ድርቅና ወረርሽኝ የመሳሰሉ የተፈጥሮ አደጋዎች በሚያጋጥሙበት ወቅት ግንባር ቀደም በመሆን እያበረከተ ስላለው ድጋፍ አድናቆታቸውን ገልጸዋል።

የሚስዮኑ ኃላፊ፣ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና ሌሎች ተያያዥ መስሪያ ቤቶች ድርጅታቸው  ኃላፊነቱን ለመወጣት በሚያደርገው እንቅስቃሴ ወቅት ላደረጉላቸው ትብብር ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

የስራ ኃላፊው ቀይ መስቀል እስካሁን በትግራይ ክልል ባከናወናቸው ተግባራት ደስተኛ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ ያጋጠሟቸውን ችግሮችንም አንስተዋል።

አቶ ደመቀ በትግራይ ክልል የሰብአዊ ዕርዳታ ተደራሽ እንዲሆን መንግስት  በትኩረት እየሰራ መሆኑንም አስገንዝበዋል።

በሁለተኛ ዙር መርሃግብር ለ2 ነጥብ 7 ሚሊየን ዜጎች ሰብአዊ ድጋፍ መደረጉንም ጠቅሰዋል።

የፀጥታ ስጋት ባሉባቸው ውስን ቦታዎች ጭምር መከላከያ ሰራዊት ከሲቪል ጋር በመቀናጀት ድጋፍ እየተሰጠ እንደሆነ መናገራቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጽ/ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።