አዋሽ ባንክ አጠቃላይ ሀብት 183 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር መድረሱን አስታወቀ

አዋሽ ባንክ

ኅዳር 17/2015 (ዋልታ) አዋሽ ባንክ አጠቃላይ ሀብቱ 183 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር መድረሱን አስታወቀ።

ባንኩ ይህንን ያስታወቀው እያካሄደ ባለው የባለ አክሲዮኖች መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ እና 17ኛውን አስቸኳይ ጉባኤ ነው።

አዋሽ ባንክ በተያዘው በጀት ዓመት ከመሰረታዊ ተቀማጭ አንፃር በተቀማጭ ገንዘብ የ41 በመቶ እድገት በማስመዝገብ 152 ቢሊየን ማግኘቱን አስታውቋል።

በተጨማሪም በውጭ ምንዛሬ ግኝት 1 ቢሊየን 343.5 ሚሊየን ዶላር ማግኘት መቻሉም ተገልጿል።

በጉባኤው ማህበራዊ ኃላፊነቱን በመወጣቱ ረገድ በሀገሪቱ በድርቅ የተጎዱ አካባቢዎችን በማገዝና የስራ እድል በመፍጠር ኃላፊነቱን እየተወጣ እንዳለ ተወስቷል።

በተጨማሪም በሀገሪቱ ከሚገኙ 10 ትልልቅ ግብር ከፋዮች መካከል አንዱ እንደሆነም ተነግሯል።

ባንኩ በመንግስት የሚሰሩ ፕሮጀክቶችን በመደገፍ ከ100 ሚሊየን ብር በላይ እገዛ ማድረጉም ተጠቁሟል።

አዋሽ ባንክ በኢትዮጵያ ዘመናዊ ቀልጣፋ የባንክ አገልግሎት በመስጠት የራሱን ሚና እየተወጣ እንደሚገኝም ተመላክቷል።

በዙፋን አምባቸው

ለፈጣን መረጃዎች፦
ፌስቡክ https://bit.ly/3Ma7QTW