አየር መንገዱ የተሻለ አፈጻጸም ላስመዘገቡ የጉዞ ወኪሎችና አስጎብኚ ድርጅቶች እውቅና ሰጠ

ሐምሌ 30/2015 (ዋልታ) የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተሻለ አፈጻጸም ላስመዘገቡ የጉዞ ወኪሎች እና አስጎብኚ ድርጅቶች እውቅና ሰጠ።

በመርኃ ግብሩ የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር)፣ የቱሪዝም ሚኒስትር አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ፣ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው እንዲሁም የተለያዩ የጉዞ ወኪል እና የአስጎብኚ ድርጅቶች ኃላፊዎች ታድመዋል።

የእውቅና መርኃ ግብሩ በየዓመቱ የሚካሄድ ሲሆን በዋናነት የቱሪዝም ዘርፍን ማነቃቃት ላይ ዓላማ ያደረገ ነው ተብሏል፡፡

በዚህም በስምንት ዘርፍ ለታጩ የጉዞ ወኪሎች እና አስጎብኚ ድርጅቶች እውቅና መሰጠቱን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ከፍተኛ ሽያጭ ላስመዘገቡ፣ ታማኝነታቸውን በተግባር ላሳዩ እንዲሁም ዲጂታላይዜሽን ላይ የተሻለ ስራ ላከናወኑ ድርጅቶች እውቅና ተሰጥቷል፡፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው በዚሁ ጊዜ አየር መንገዱ የአየር ትራንስፖርትን ከማቀላጠፍ ባሻገር ለቱሪዝም እድገት የበኩሉን ሚና እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል፡፡