አፍሪካ በታዳሽ ሃይል ዘርፍ ያላትን አቅም መጠቀም ከቻለች የዜጎችን የሃይል ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ትችላለች – ኢንጂነር ስለሺ በቀለ (ዶ/ር)

አፍሪካ በታዳሽ ሃይል ዘርፍ ያላትን እምቅ አቅም መጠቀም ከቻለች የዜጎችን የሃይል ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደምትችል የኢፌዴሪ የውሃ፣ መስኖና ኢነርጅ ሚኒስትር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡

ሚኒስትሩ በዓለም አቀፉ የውሃ አካላት ምህንድስና እና ምርምር ማህበር 85ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ላይ በዌቢናር ተሳትፈዋል፡፡

በዚህ ወቅት ባደረጉት ንግግር 90 በመቶ የሚሆነው የዓለማችን ታዳሽ ኃይል ከውሃ ግድቦች እንደሚመነጭ ጠቅሰው፥ አፍሪካም በዘርፉ ያላትን እምቅ አቅም መጠቀም ከቻለች የዜጎችን የኃይል ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ትችላለች ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ ታላቁን የህዳሴ ግድብ እየገነባች ነው ያሉት ሚኒስትሩ፥ ግድቡ ከኤሌክትሪክ ኃይል በተጨማሪ ለስራ እድል ፈጠራ፣ ኢንዱስትሪዎችን ለማስፋፋት፣ በኃይል አቅርቦት እጥረት ምክንያት በሴቶች ላይ የሚደርሰውን እንግልት ለመቀነስ ብሎም ለውጭ ምንዛሬና እና ከጎረቤት ሃገራት ጋር የተሳሰረ ኢኮኖሚን ለመፍጠር እንደሚያስችልም አውስተዋል፡፡

ማህበሩ በሃይድሮ መካኒክስና ሃይድሮሊክ ምህንድስና አተገባበር ላይ ምርምሮችን በማካሄድ ዓለም አቀፍ ትብብርን የማጎልበት አላማ ይዞ መነሳቱን ከውሃ፣ መስኖና ኢነርጅ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡