ኤጀንሲው በአማራ ክልል ለተፈናቀሉ ወገኖች ድጋፍ አደረገ

መስከረም 25/2014 (ዋልታ) የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ በአማራ ክልል  በአሸባሪዉ የትህነግ ቡድን ከቤት ንብረታቸዉ ለተፈናቀሉ ወገኖች የ15 ሚሊየን ብር ድጋፍ አደረገ፡፡

የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሹመቴ ግዛዉ ÷ይህ ድጋፍ በመላው የተቋሙ አመራርና አባላት ስም በመደረጉ  መደሰታቸውን ገልፀው በየትኛዉም ክልል የሚደርስ ጉዳት የኛም ጉዳት ነዉ ብለዋል።

ከዚህ ቀደም የኤጀንሲዉ አባላት የአንድ ወር ደሞዛቸዉን ለመከላከያ ሠራዊት ደጋፍ ከማድረጋቸውም ባሻገር ደም መለገሳቸውን  አስታውሰው  ከዚህ ባለፈ የኤጀንሲዉ አባል ሆነዉ የመዝመት ጥያቄ ላቀረቡ አባላትም  አስፈላጊዉ ቅድመ ዝግጅት ተደርጎ መላካቸውን ገልጸዋል።

በቀጣይም በጦርነቱ ጉዳት ለደረሰባቸዉ ሌሎች ክልሎች ኤጀንሲው ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል።

የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ይልቃል ከፍያለዉ በበኩላቸዉ ÷በወራሪዎች ግፍ  የተነሳ ስቃይ እና እንግልት እየደርሰበት ለሚገኘው ህዝብ ኤጀንሲዉ ድጋፍ በማድረጉ በአማራ ክልል ህዝብ ፣ በክልሉ መንግስት ስም እና በተፈናቃዮቹ ስም ምስጋና አቅርበዋል።

በአሁኑ ሰዓት 500 ሺህ የሚደርሱ ሰዎች ከቤት ከቀያቸው መፈናቀላቸዉን ርእሰ መስተዳደሩ ገልጸው÷ በኤጀንሲው የተደረገው ድጋፍ ተፈናቃዮቹን ወደነበሩበት ቀዬና አኗኗር ለመመለስ  አሰተዋጽኦ ያበረክታል ማለታቸውን ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡