የአፍሪካ ሕብረትና የአለም ሠራተኞች ድርጅት በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት ተፈራረሙ

የካቲት 4/2014 (ዋልታ) የአፍሪካ ሕብረትና የአለም ሠራተኞች ድርጅት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል።

ስምምነቱን የአለም ሠራተኞች ድርጅት የአፍሪካ ቀጠና ረዳት ዋና ዳይሬክተር ሲንቲያ ሳሙኤል ኦሎንጁን በአፍሪካ ሕብረት የጤና፣ የሰብአዊ መብትና የማህበራዊ እድገት ጉዳዮች ኮሚሽነር ሚናታ ሴሱማ ሰማቴ ጋር ተፈራርመውታል።

የአለም ሠራተኞች ድርጅት የአፍሪካ ቀጠና ረዳት ዋና ዳይሬክተር ሲንቲያ ሳሙኤል ኦሎንጁን ከአፍሪካ ሕብረት ጋር የረጅም ጊዜ ትስስራችንን የሚያጠናክር ስምምነት ተፈራርመናል ብለዋል።

ስምምነቱ በአፍሪካ አህጉር ሊተገበር የታቀደውን የ2063 አጀንዳ ለማስፈጸም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋልም ነው ማለታቸውን የኢዜአ ዘገባ አመልክቷል።

አክለውም ስምምነቱ የተመድ የ2030 ቀጣይነት ያለው የእደገት አጀንዳን እንዲሁም ለሁሉም አፍሪካውያን ማኅበራዊ ፍትህን ማስፈን የሚለውን የ2019ኙን የአቢጃን አዋጅ ለማስፈጸም ያግዛል ሲሉ ገልጸዋል።