የ4ጂ ኤልቲኢ ፈጣን አገልግሎት በአሶሳ ተጀመረ

መስከረም 20/2014 (ዋልታ) – ኢትዮ-ቴሌኮም በምዕራብ ምዕራብ አራተኛው ትውልድ (4ጂ) ኤልቲኢ አድቫንስድ ፈጣን የሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት መስጠት ጀመረ።

አገልግሎቱ በአሶሳ፣ ባምባሲ፣ ግልገል በለስ፣ እንዲሁም በታላቁ የህዳሴ ግድብ የኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑ ተገልጿል።

የኢትዮ- ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ካምፓኒው ከፍተኛ የዳታ አጠቃቀም በሚታይባቸው የሃገሪቱ ከተሞች የ4ጂ ፈጣን አገልግሎት ለማስፋፋት እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡

በምዕራብ ምዕራብ ሪጅን የተጀመረው የ4ጂ አገልግሎትም 108 ሺሕ ገደማ ደንበኞችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡

እስካሁን ኢትዮ ቴሌኮም በተገበረው 4ጂ ኤልቲኢ አድቫንስድ ፈጣን የሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ማስፋፋያ በ16 ሪጅኖች 92 ከተሞችን ተደራሽ ማድረጉም ተገልጿል፡፡

የካምፓኒው አገልግሎት መስፋፋትም ዲጂታል ኢኮኖሚ ለመገንባት የጎላ ፋይዳ እንዳለውም ተናግረዋል::

(በሄብሮን ዋልታው)