የህንድ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ለመሰማራት ፍላጎት አላቸው

የህንድ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ለመሰማራት ፍላጎት እንዳላቸው ገለፁ።

ፕሬዝዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ የህንድ ባለሃብቶች የልዑካን ቡድንን ትናንት በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።

የልዑካን ቡድኑ በኢትዮጵያ ያለውን የኢንቨስትመንት አማራጮች ለመመልከትና ከመንግስት ጋር ውይይት በማድረግ ወደ ተግባር ለመግባት ዓላማ አድርገው መምጣታቸውን የፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤት የፕሮቶኮልና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አሸብር ጌትነት ገልጸዋል።

ባለሃብቶቹ በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋያቸውን በሚያፈሱበት ወቅት በመንግስት በኩል አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚደርግ ፕሬዝዳንት ዶክተር ሙላቱ መናገራቸውንም አቶ አሸብር ተናግረዋል።

የልዑካን ቡድኑ ተወካይ ሚስተር ሚሊንድ ሳህ እንዳሉት፤ ባለሀብቶቹ በኢትዮጵያ ያለውን የኢንቨስትመንት አማራጮች በመመልከት በተለያዩ ዘርፎች የመሰማራት ፍላጎት አላቸው።

ኢትዮጵያ እና ህንድ እ.ኤ.አ ከ1948 ጀምሮ የሁለትዮሽ ግንኙነት ያላቸው ሲሆን ሁለቱ አገሮች በ1952 በአዲስ አበባ እና ኒው ዴልሂ ኤምባሲያቸውን ከፍተዋል።(ኢዜአ)