ተማሪዎች ምክንያታዊ ያልሆኑ ጥያቄዎችን ወደ ብሄር ግጭት ከሚለውጡ አካላት ራሳቸውን እንዲጠብቁ ጥሪ ቀረበ

የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ምክንያታዊ ያልሆኑ ጥያቄዎችን ወደ ብሄር ግጭት ከሚለውጡ አካላት ራሳቸውን ሊጠብቁ እንደሚገባ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አሳሰበ።

ዩኒቨርሲቲዎች የልህቀት ብቻ ሳይሆን የባህል ልውውጥ ትልቅ መድረኮች መሆናቸው እሙን ነው።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ጥላቻ እና ልዩነትን የሚዘሩ አካላት እነዚህን ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ኢላማ አድርገው ሁከት እና ግርግር እንዲነሳ ሲጥሩ ተስተውለዋል።

ተቋማቱን ከምርምር ማዕከልነት ወደ ግጭት መናኸሪያነት ለመለወጥ የሚንቀሳቀሱ ሀይሎች ምክንያታዊ ያልሆኑና የግለሰብ ጉዳዮችን አግዝፈው ወደ ብሄር እና ሀይማኖት ተኮር ግጭት ሲቀይሩም ታይቷል።

ጣቢያችን ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አዲስ ገቢ ተማሪዎችም፥ አሁን ላይ የጥፋት ተልዕኮ ካነገቡ ሀይሎች ራሳችን ልንጠብቅ ይገባል ይላሉ።

መከባበር እና አብሮነትን ማስቀጠል ቀዳሚው ተግባር መሆን እንዳለበትም ያነሳሉ።

ተማሪዎች በግቢ ቆይታቸው ጥያቄ እና ሀሳባቸውን በዴሞክራሲያዊ እና ሰላማዊ በሆነ መንገድ መግለፅ እንዳለባቸው ጠቅሰው፥ ለሚነሱ ጥያቄዎችም አፋጣኝ ምላሽ መስጠት እንደሚገባም ተናግረዋል።

በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሀሳብ በነፃነት የሚንሸራሸርበት ለሀገር እና ወገን የሚበጁ ጉዳዮች የሚመከሩበት መድረክ ሊመቻች ይገባል ባይ ናቸው፤ የትምህርት ዘመኑ በሰላም እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን እንደሚወጡ በመጥቀስ።

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የውጭ ግንኙነት፣ ትብብር እና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር ዶክተር ደመቀ አጭሶ በበኩላቸው፥ የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ምክንያታዊ በሆነ የሀሳብ ሙግት እንደሚያምኑ ይናገራሉ።

ዩኒቨርሲቲው በቀጣይም የመማር ማስተማሩ ሂደት ሰላማዊ ሆኖ እንዲቀጥል እና ተማሪዎች የሚያነሷቸው ጥያቄዎች በሚፈቱበት ሁኔታ ተከታታይ ምክክሮችን ያደርጋልም ነው ያሉት።

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በነገው እለት በመማር ማስተማር ሂደቱ እና የሀገሪቱን ሰላም አስጠብቆ ማስጠቀል በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ለአዳዲስ ተማሪዎቹ ገለጻ ያደርጋል።

በዩኒቨርሲቲው ተምረው ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሱ ሰዎችም የማነቃቂያ መልዕክት ያስተላለፋሉ ተብሎ ይጠበቃል።(ኤፍቢሲ)