ዩጋንዳ 3ሺህ የደቡብ ሱዳን ዜጎች ወደ ሀገሯ መግባታቸውን ገለጸች

ዩጋንዳ ወደ 3ሺህ የሚጠጉ የደቡብ ሱዳን ዜጎች የሀገራቸው የመንግሥት ጦር አባላት በአንድ የድንበር ከተማ ላይ የሰነዘሩትን ጥቃት ሸሽተው ትናንት ወደ ሀገሯ መግባታቸውን ገለጸች ።

በሀገሩ ብዙ ስደተኞችን በማስተናገዱ ለሚታወቀው የዩጋንዳ መንግሥት ይህ ሁኔታ ትልቅ ተግዳሮት ሆኖበታል።

ምክንያቱም ስደተኞች አሁን በብዛት ሀገሩ በገቡበት ሁኔታ የተነሳ ለሁሉም ስደተኞች እንደሚፈለገው ርዳታ ለማቅረብ አቅሙ እና ገንዘብ እንደጎደለው አስታውቋል። 
የደቡብ ሱዳን መንግሥት ወታደሮች ከዩጋንዳ ጋር በሚያዋስነው ድንበር አካባቢ በሚገኘው የፓጆክ ከተማ ላይ ጥቃት በመሰንዘር ብዙዎችን መግደላቸው ተሰምቷል።

ወደ 3,000 የሚጠጉ የደቡብ ሱዳን  ዜጎች የሱዳን ህዝብ አፃ አውጪ ጦር ባለፈው ሰኞ በተፈጸመው ጥቃት ሸሽተው ትናንት ወደ ጎረቤት ዩጋንዳ ተሰደዋል ። 
ዩጋንዳ በዓለም ብዙ ስደተኞችን የምታስተናግድ ሀገር ናት፣ በቢዲ ቢዲ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ብቻ 274ሺህ  ስደተኞች ይገኛሉ።

በዚህ ወር ብቻ 800ሺህ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች ዩጋንዳ የገቡ ሲሆን፤ ይህ በሀገሪቱ ስደተኞችን የማስተናገድ አቅም ላይ ትልቅ ተግዳሮት ደቅኗል።

ይኸው አዲሱ የስደተኞች እንቅስቃሴ ሰሞኑን በፈነዳው ውጊያ ሰበብ ብቻ ሳይሆን በሀገሪቱ በተከሰተውም ረሀብ እና እየወደቀ ባለው የኤኮኖሚ ሁኔታም ምክንያት ነው።

ይኸው ሁኔታ የዩጋንዳን መንግሥት እና የርዳታ ድርጅቶችን አሳስቧል።

«ዩኤንኤችሲአር» በዩጋንዳ መጠለያ ጣቢያዎች ያሉትን ስደተኞች በጠቅላላ ለመርዳት ቢያንስ 782 ሚልዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ የግብረ ሰናዩ ድርጅት «ዎርልድ ቢዥን» የዩጋንዳ ቅርንጫፍ ኃላፊ ጂልበርት ካማንጋ ከሰሜን ዩጋንዳ ለዶይቸ ቬለ ገልጸዋል፡፡

ብዙዎቹ የርዳታ ድርጅቶች ስራቸውን ማከናወን አልቻሉም።
« ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በዩጋንዳ ያሉትን ስደተኞች ለመርጃ እንደሚፈለገው ርዳታ እየሰጡ አይደለም።  የዩጋንዳ መንግሥት ድጋፍ የሚሞገስ ቢሆንም፣ ስደተኞቹን ያስተናግድ ዘንድ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ድጋፍ እንዲያደርግለት ጥሪ እናቀርባለን። ምክንያቱም፣ በዩጋንዳ ያሉት የርዳታ ድርጅቶች በጠቅላላ የበጀት እጥረት አጋጥሟቸዋል። »
በዚሁ ሰበብም ስደተኞች በቂ ርዳታ አልቀረበም በሚል ቅሬታ እያሰሙ መሆኑን ገልጿል።

ዩጋንዳ ስደተኞችን ማስተናገዷን እንደምትቀጥል ሮበርት ቢገልጹም፣ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የደቡብ ሱዳን ውጊያ የሚያበቃበትን እና ስደተኞች ወደ ትውልድ ሀገራቸው የሚመለሱበትን መንገድ መንገድ ቢያፈላልግ መልካም እንደሚሆን አስታውቀዋል።

ከደቡብ ሱዳን ስደተኞች መካከል 86% ሴቶች እና ህፃናት ናቸው። ምንጭ -www.Dw/com