የአይ ኤስ ቁልፍ መሪ አቡ ሙሀመድ አል አድናኒ መገደሉ ተሰማ

የፅንፈኛው ቡድን እስላሚክ ስቴት ቁልፍ የስትራቴጂ አማካሪ እና መሪ አቡ ሙሀመድ አል አድናኒ በሶሪያ መገደሉ ተሰማ።

የሽብር ቡድኑ በሶሪያ እና ኢራቅ ከፍተኛ ወታደራዊ ኪሳራ በደረሰበት ማግስት ነው የመሪው ሞት ዜና የተሰማው።

ለአይ ኤስ ቅርብ የሆነው አማቅ የዜና ወኪል እንደዘገበው፥ አድናኒ በአሌፖ ግዛት ነው የተገደለው።

አማቅ በረመዳን ፆም ወር በምዕራባውያን ሀገራት የተለያዩ ጥቃቶች እንዲደርሱ ስላደረገው አድናኒ አሟሟት ያለው ነገር የለም።

ፔንታጎን በበኩሉ አድናኒን ኢላማ ያደረገ የአየር ላይ ጥቃት በአል ባብ ከተማ መሰንዘሩንና ውጤቱም እየተመረመረ መሆኑን አስታውቋል።

የፔንታጎን ቃል አቀባይ ፒተር ኩክ አድናኒንየአይ ኤስ ውስጣዊ ኦፕሬሽን ዋነኛ መሀንዲስ ነውበማለት ገልፀውታል።

አይ ኤስ አሜሪካ መራሹን የአየር ላይ ጥቃት በሚደግፉ ሀገራት ላይ የሽብር ጥቃት እንደሚያደርስ በተለያዩ ጊዜያት በድምፅ መልዕክት ያስተላለፈው አድናኒ፥ ለመጨረሻ ጊዜ ድምፁ የተሰማው ባለፈው ግንቦት ወር ላይ ነበር።(ኤፍ ቢ ሲ)