በአሜሪካ ድንበር የስድስት ስደተኛ ሕፃናት ሕይወት ማለፉ ተገለጸ

ባለፉት ስምንት ወራት ብቻ በአሜሪካ የድንበር ተቆጣጣሪዎች በቁጥጥር ሥር ከዋሉ በኋላ ስድስት ስደተኛ ሕፃናት ሕይወታቸው ማለፉ ተገልጿል።

ከኤል ሳልቫዶር የመጣች የ10 ዓመቷ ታዳጊ በአሜሪካ የስደተኞች ማቆያ ውስጥ ባለፈው ዓመት ነበር ሕይወቷ ያለፈው።

ባለስልጣናት እንዳስታወቁት ታዳጊዋ የልብ ሕመም ያለባት ሲሆን፣ ባለፈው መስከረም ወር ናብራስካ ሆስፒታል ሕክምና እየተደረገላት ሕይወቷ አልፏል።

ታዳጊዋ በቴክሳስ ሳን አንቶኒዮ ስደተኞች ካምፕ የገባች መሆኗን የጤናና የደህንነት አገልግሎት ክፍል ቃል አቀባይ ማርክ ዌበር በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል። በክፍሉም የጤና ክትትል ሲደርግላት ነበር።

ምንነቱ ያልተገለፀው የቀዶ ሕክምና የተደረገላት ሲሆን ከዚያ በኋላ ለተጨማሪ የጤና ችግር ተዳርጋለች፤ በግንቦት ወር ከሆስፒታል ከወጣች በኋላም ወደ አሪዞና የህፃናት ማቆያ ተዛውራለችም ነው የተባለው።

መስከረም ወር ላይ ለቤተሰቦቿ እንድትቀርብ በሚል ምክንያት ከዚያ ወጥታ ወደ ናብራስካ የህፃናት ማቆያ ተልካለች። በከፍተኛ ትኩሳትና የአተነፋፈስ ችግርም ከሦስት ቀናት በኋላ ሕይወቷ እንዳለፈ ዌበር ተናግረዋል።

ባላሰልጣናቱ መሞቷን ይፋ ማውጣት ያልፈለጉ ሲሆን፣ ከአውሮፓውያኑ 2010 ወዲህ ሕፃን ስደተኛ በአገሪቱ የስደተኞች ማቆያ ሕይወቱ ሲያልፍ ታዳጊዋ የመጀመሪያዋ ናትም ተብሏል።

የታዳጊዋ ስም እና ድንበር ተሻግራ እንዴት ወደ አሜሪካ እንደገባች የተባለ ነገር የለም። ይሁን እንጂ ዲሞክራቶች የሞቷን ምክንያት ለማጣራት ምርመራ እንዲደረግ ጠይቀዋል።

ባሳለፍነው ሰኞም ከጓቲማላ የመጣው የ16 ዓመቱ ሕፃን በቴክሳስ በሚገኘው ማቆያ ውስጥ ሕይወቱ ማለፉ የሚታወቅ ሲሆን ጉዳዩ ተሸፋፍኖ ቀርቷል።

ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካና ሜክሲኮን ድንበር አልፈው ወደ አሜሪካ የሚገቡ ሕገወጥ ስደተኞች ላይ ቁርጠኛ ውሳኔ ካሳለፉ በኋላ ድንበሩን ለማቋረጥ የሚሞክሩ ሰዎች ቁጥር ጨምሯል።

ከባለፈው ጥርና ሚያዚያ ወር ብቻ በአሜሪካና ሜክሲኮ ድንበር ከ300 ሺህ በላይ ስደተኞች እንደሚገኙ የአገሪቱ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል። ቁጥሩም ከወር ወር እየጨመረ ነው የተባለው።

ባለሥልጣናቱ ቁጥሩ እየጨመረ በመምጣቱ መሠረታዊ ፍላጎታቸውን እንኳን ማሟላት እንዳልቻሉ ገልፀው ስደተኞቹ በአብዛኛው ከጓቲማላ፣ ሆንዱራስ እና ኤል ሳቫዶር የሚመጡ ናቸው ብለዋል። ብዙዎቹም ስደተኞች በግጭትና በድህነት ምክንያት አገራቸውን ጥለው የወጡ ሲሆን በአሜሪካ ጥገኝነት የሚፈልጉ ናቸው። (ምንጭ፡-ቢቢሲ)