ልማት ባንክ በዘንድሮ የበጀት 14 ቢሊዮን ብር ብድር ለመሥጠት ማቀዱን አስታወቀ

የኢትዮጵያ ልማት  ባንክ  በዘንድሮ የበጀት ዓመት  14 ቢሊዮን   ብር ብድር  ለመሥጠት   መዘጋጀቱን   አስታወቀ ።

የባንኩ ስትራቴጂክ ለውጥና ኮሚኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ክፍሌ ኃይለየሱስ ለዋሚኮ እንደገለጹት በዘንድሮ የበጀት ዓመት ባንኩ በፕሮጀክቶች ብድርና በሊዝ ፋይናንሲንግ   የብድር ሥርዓቱ   በአጠቃላይ  የ14ነጥብ 03 ቢሊዮን ብር ብድርን በማጽደቅ ለተጠቃሚዎች ለማቅረብ ተዘጋጅቷል ።

ባንኩ ባለፈው የበጀት ዓመት በአጠቃላይ 12 ነጥብ 07 ቢሊዮን ብር ብድር መሥጠቱን ያስታወሱት አቶ ክፍሌ በዘንድሮ የበጀት ዓመት  ባንኩ  የሚሠጠውን የብድር  መጠን  ወደ 14  ነጥብ 0 3 ቢሊዮን ብር ማሳደጉን ተናግረዋል ።

በዘንድሮ ዓመት ባንኩ በአገሪቱ የኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ሽግግርን ሊያፋጥኑ በሚችሉ ዘርፎች  ላይ  ለሚሠማሩ  ፕሮጀክቶችና ኢንተርፕራይዞች የብድር አገልግሎት እንዲያገኙ  ትኩረት  ሠጥቶ እንደሚሠራ አቶ ክፍሌ አመልክተዋል ።

መንግሥት የአገሪቱን አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪ ዘርፍን ድጋፍ ለማድረግ ባስቀመጠው የልማት አቅጣጫ  መሠረት በዘንድሮ  የበጀት  ዓመት ባንኩ በዘረጋው የሊዝ ፋይናንስ ብድር ሥርዓት መሠረት በአጠቃላይ ለማሽነሪ ግዠ 4 ነጥብ 12 ቢሊዮን ብር ለመፍቀድ መዘጋጀቱን አቶ ክፍሌ  ተናግረዋል ።  

እንደ አቶ ክፍሌ ገለጻ በዘንድሮ የበጀት ዓመት ባንኩ  ከተበዳሪዎች   5ነጥብ  67  ቢሊዮን  ብር  ለመሰብሰብ  ማቀዱንና አጠቃላይ   የባንኩን የብድር መጠን  ወደ  40 ነጥብ 8  ቢሊዮን   ብር ለማድረስ   እየተንቀሳቀሰ ይገኛል  ።

ባንኩ  በዘረጋው  የሊዝ ፋይናንስ  አሠራር ከፕሮጀክት አነስ የሚሉና  በአነስተኛና ቁጠባ ተቋማት መስተናገድ የማይችሉ አነስተኛና መካከለኛ  ደረጃ ላይ ለሚገኙ  ኢንተርፕራዞች  ከ1ነጥብ5  እስከ 30  ሚሊዮን  ብር ብድር እየሠጠ መሆኑ ተመልክቷል ።

የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በ2009 የበጀት ዓመት ከፕሮቪዥንና ከታክስ በኋላ የ323.85 ሚሊዮን  ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን  ይታወሳል ።