አትክልት እና ፍራፍሬን አዘውትሮ መመገብ የኩላሊት ታማሚዎች የህክምና ወጪን ይቀንሳል

በአለም ዙሪያ በርካቶች ለኩላሊት ህመም የተጋለጡ ሲሆን፥ ለህክምናው ሲሉ በርካታ ገንዘብ ሲያፈሱ ይስተዋላል።

ታዲያ ከሰሞኑ አዲስ የወጣ ጥናት የኩላሊት ህመምተኞች አትልክት እና ፍራፍሬን አዘውትረው የሚመገቡ ከሆነ የህክምና ወጪያቸውን ከግማሽ በላይ መቀነስ ይችላሉ ይላል።

በቴክሳስ ዩኒቨርሲቲ ጥናቱን ያካሄዱት ተመራማሪዎች፥ የተስተካከለ አመጋገብ የደም ግፊትን ለመቆጣጠር እና ለህክምናው የሚወጣውን ወጪ ይቀንሳል ብለዋል።

በህመም የተጠቃ ኩላሊት አሲድ የማስወገድ አቅሙ የሚዳከም ሲሆን፥ ይህም “ሜታቦሊክ አሲዶሲስ” ወይም ከፍተኛ የሆነ የአሲድ ክምችት በደም ውስጥ እንዲከማች የሚያደርግ ነው።

ይህንን ለማከምም “ሶዲየም ባይካርቦኔት” መውሰድ ወይም ደግሞ ወደ ህክምና ተቋም በየጊዜው በመሄድ ህክምና መከታተል የግድ ነው ተማራማሪወዎች።

አሁን በተሰራው ጥናት ግን በኩላሊት ህመም የተጠቁ ሰዎች “ሶዲየም ባይካርቦኔት” መውሰድ ሳይጠበቅባቸው አትልክት እና ፍራፍሬን ብቻ በመመገብ በደማቸው ውስጥ ያለውን የአሲድ መጠን መቀነስ እንደሚችሉ አረጋግጠናል ይላሉ ተመራማሪዎች።

በጥናቱ ላይ በኩላሊት ህመም የተጠቁ 108 ሰዎች የተካፈሉ ሲሆን፥ በዚህም ተሳታፊዎቹን ለሶስት በመክፈል ሶዲየም ባይካርቦኔት እንዲወስዱ፤ ሌሎች ደግሞ ህክምና እንዲከታተሉ ቀሪዎቹ ደግሞ አትልክት እና ፍራፍሬን አዘውትረው እንዲመገቡ ነበር የተደረገው።

በጥናቱ ተካፋዮች ላይ ለ5 ዓመታት ክትትል ሲደረግ የቆየ ሲሆን፥ በዚህም አትክልት እና ፍራፍሬን አዘውትረው የሚወስዱ ሰዎች ሶዲየም ባይካርቦኔትን ከሚወስዱት እና በየጊዜው ህክምናን ከሚከታተሉት ይልቅ የደም ግፊታቸው መጠን ቀንሶ ታይቷል።

በዚህም ይላሉ ተመራማሪዎቹ በአትክልት እና ፍራፍሬ አማካኝነት አሲድ በኩላሊታችን ውስጥ እንዳይከማች በማድረግ የደም ግፊታችን የተስተካከለ እንዲሆን ይረዳናል ይላሉ።

በተጨማሪም ይላሉ ተመራማሪዎቹ አትክልት እና ፍራፍሬን አዘውትረው የሚመገቡ ሰዎች ሶዲየም ባይካርቦኔት ከሚወስዱት እና በየጊዜው መደበኛ ህክምና ከሚከታተሉ ታማሚዎች ጋር ጋር ሲነጻጸሩ ለህክምና የሚያወጡት ወጪም እጅጉን የቀነሰ ነው።

ለዚህም እንደ ማሳያ ያስቀመጡት ተመራማሪዎቹ በ5 ዓመት ጊዜ ውስጥ ህክምናን ሲከታተሉ የነበሩ ሰዎች ወጪያቸው 152 ሺህ 305 የአሜሪካ ዶላር ሲሆን፥ ሶዲየም ባይካርቦኔት ሲወስዱ የነበሩት ገድሞ 155 ሺህ 372 የአሜሪካ ዶላር ነው ያወጡት ተብሏል።

አትልክት እና ፍራፍሬን ሲመገቡ የነበሩ ሰዎች ግን ጤንነታቸውን ለመጠበቅ አጠቃላይ ያወጡት ወጪ 79 ሺህ 760 የአሜሪካ ዶላር ነው ሲሉም ተመራማሪዎቹ ያስረዳሉ።

ዶክተር ኒምሪት ጎራያ፥ አዲስ የተገኘው ጥናት በዘርፉ ትልቅ ስኬት ነው፤ ሰዎች አመጋገባቸውን እንዲቀይሩ ሳናስገድድ በቀላሉ ጤንነታቸውን እንዲጠብቁ ለማድረግ ያስችላል ብለዋል።

ሰዎች በእለት ምግባቸው ውስጥ ለጤና ጠቃሚ ናቸው የተባሉትን አራት እትክልት እና ፍራፍሬ አካተው በመመገብ ብቻ ለህክምና እና መድሃኒት ለመግዛት የሚያወጡትን ወጪ በቀላሉ መቀነስ ይችላሉም ብለዋል። (ኤፍ.ቢ.ሲ)